የ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ደራሲዎች

ስለ ኢትዮጵያ ደራስያን

(ክፍል 3)

በተአምራት አማኑኤል

[1936 ዓ.ም]

(… ከክፍል ሁለት የቀጠለ)

የ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ደራሲዎች

፩ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ገብረ የሱስ

አለቃ ታየ ሲጽፉና ሲያስተምሩ በነበሩበት ጊዜ፣ ፊት ኤውሮጳ ኋላም ኢትዮጵያ ሁነው ላማርኛ አጻጻፍና ንግግር ብዙ ትጋት ያሳዩ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ገብረ የሱስ ናቸው። በወጣትነታቸው ለትምህርት ወደ ኤውሮጳ በመሔዳቸው፣ በነገር አስተያየትም መልክ ባለው ንግግር አሳብን በጽሕፈት በመግለጥ ልዩ ስጦታ ያላቸው ደራሲ ናቸው። የሕይወታቸው ታሪክ ግን እጅግ የሚያሳዝን ነው።

የዛሬ 50 ዓመት አቅራብያ ዕድለኛ ሁነው ከጃንሆይ ካጤ ምኒልክ ተመርጠው ለትምህርት ወደ ኤውሮጳ ተላኩ። የጣልያን የጦር አለቃ ባራቲዬሪ (1888 ዓ.ም) መልሶ ወደ ሮማ እስኪልካቸው ድረስ፣ ከኢትዮጵያ ጠላት ጋር ተሰልፈው ዓዲግራት ድረስ መጡ። ኢትዮጵያ ይህን ሁሉ ሳትረሳ፣ ይቅርታ አድርጋ፣ በልጅ ኢያሱ አልጋ ወራሽነት ጊዜ ለትልቅ ሥራ አጨቻቸው።

ለዚህ ወረታ ወጣቱን የኢትዮጵያን አልጋ ወራሽ ልጅ ኢያሱን በሚያምር ንግግር በማሞገስ ደስታቸውን ገለጡ። በእውነትም ልጅ ኢያሱ ባልሆኑ ካጤ ምኒልክ ጋራ የሠሩት መሳፍንትና መኳንንት ሁሉ ተቀይመዋቸው ነበር። አሳባቸውም የነበረ በቤተ መንግሥት ሥራ ለማስያዝ ይቅርና የኢትዮጵያን መሬት እንዳይረግጡ ለማድረግ ነበር። የኢትዮጵያ ባላባቶች የልጅ ኢያሱ ሥራ አጀማመር ብዙ የሚያሠጋ ሁኖ ታይትዋቸው ሥልጣናቸውን እንዲያስረክቡ ባስገደድዋቸው ጊዜ፣ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ከዚያ ሁሉ ሰው አብልጠው ለኢትዮጵያ የተቈረቈሩ መሆናቸውን ለማስረዳት፣ የሚያምረውን ግጥማቸውን የልጅ ኢያሱ መስደቢያ በማድረጋቸው አበላሹት።

እንኳን ይህን፣ ከጠላት ጋር አገራቸውን ሊወጉ የተሰለፉትን በደል የቤተ መንግሥት አስተዳደሮች ትተውላቸው ነበር። አሁንም ንግሥት ዘውዲቱና ጃንሆይ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አልጋ ወራሽ ሁነው የመንግሥቱን ሥራ ሲያካሒዱበት በነበረ ጊዜ፣ ከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ተቀበሉ። ከቶውንም በሚኒስትርነት ሥራ ወደ ሮም ተላኩ። ጠላት አገራችንን ሲያጠፋት፣ አሁንም ተመልሰው ለጣልያን ዋና ሠራተኛ ሆኑለት። አገርን ለያዘ ጠላት ሳያስፈልግ ማገልገል እንኳ ከመነቀፍ ቢያደርስ፣ ይህ አልበቃ ብሎ ለጠላት ታማኝነታቸውን ለመግለጥ በንጉሠ ነገሥቱ ላይ ጀምረው እስከ ተራው አርበኛ ድረስ የማይጠጋውና ያልሆነ ቃል በመጻፍ ብዕራቸውን አበላሹ።

ተራ ጸሐፊ ቢሆኑ የሚያሳዝነውን የሕይወታቸውን ታሪክ ሳላነሣው በቀረሁ። ነገር ግን ፕሮፌሰር አፈወርቅ እኛ ላለንበት ትውልድ ዋና ደራሲው ናቸው።

afework-grammarafework-grammar-2

ፕሮፌሰር አፈወርቅ ባማርኛ ከጻፍዋቸው መጻሕፍት፣ “የአጤ ምኒልክ ታሪክ” እና “ልብ ወለድ ታሪክ” ዋና ሁነው ይታዩናል። የነርሱን አኳኋን ከማስታወቃችን በፊት የአማርኛ ቋንቋ ሕጉንና ሕዝቡ የሚወደውን የንግግር ወይም ያጻጻፍ ዓይነት እናመልክት። ከሕጉም ርቀው አዲስ አካሔድ የሰጡን ደራስያንና የተለምዶውን ንግግርና አጻጻፍ ሳይለቁ ጣዕም ያለበት ለማድረግ የቻሉትን ካልቻሉት ለመለየት ይረዳናል።

የአማርኛ ቋንቋ ከብዙው ሕገጋቱ አንዱ፣ ማሰርያ አንቀጽን ከንግግር መጨረሻ ማግባት ነው። ከጽሕፈት ላይ ባንድ ማሰርያ አንቀጽ ውስጥ ባሉት ቃላት ማኽል ጣልቃ እያገባ ልዩ ልዩ አሳብና ንግግር በሚጨምርበት ጊዜ፣ ዋናውንና ጣልቃ የገባውን ከውኖ ለማስተዋል እንዲመች ሊያደርጉ የቻሉ ስጦታ ያላቸው ደራስያን ብቻ ናቸው። ደራሲው ሙሉውን ንግግር ባማርኛ ባሕርይ በሚያስኬድበት ጊዜ ደግሞ ሰነፍ አንባቢ እንዳይታክተው ለማድረግ ያሰበበት እንደሆነ፣ ንግግሩን ባጭር ባጭሩ በማሰሩ ላንባቢ መመቸቱ እርግጥ ነው።

ቢሆንም ደራሲ በፊተኛው (በረጅሙ) አካሔድ ሲጽፍ አንባቢው በውጥን ጭርስ አካሔድ አስሮ ለንግግሩ ደራሲው ያላሰበውን አሳብ ከመስጠት የሚደርስበት ጊዜ አለ። ደራሲው በሁለተኛው አካሔድ (ባጭሩ) ሲጽፍ አንባቢው አሁን ካመለከትነው ስሕተት አይደርስም። ግን ንግግሩን ባንድ ማሰሪያ አንቀጽ ሊጠቀልል ሲሽል ደራሲው እያቋረጠ በመናገር አንደበቱን ያልረታ ሕፃን ሊመስል ነው። ንግግሩንም በመጠኑ ካማርኛ ባሕርይ የራቀ ሊያደርገው ነው። ዋና ደራሲ የምንለው፣ በረጅሙም ሆነ ባጭሩ አካሔድ ጽፎ፣ ንግግሩ ግልጽ እና ጣዕም ያለው ሲሆን ነው።

afework-guide
የአፈወርቅ ገብረየሱስ “Guide de Voyage”

በኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን፣ ሲበዛም ሲያንስም በልዩ ልዩ ሕዝብ (ይልቁንም በምሥራቃውያን) የተለመደ አካሔድ በሁለት፣ በሦስት ፍች የሚተረጎም ቃል እየፈለጉ ከንግግር ማግባት ነው። እንዲህ ያለው አካሔድ “አማርኛ” ወይም “ስለምን” ይባላል። ይህም በኢትዮጵያ እጅግ የተወደደና የተለመደ ንግግር ነው። እንዲህ ያለውን ንግግር የሚያመጣንም ሰው ሁሉ የንግግር ዕውቀት ያለው ሰው በመሆኑ የሚከራከርበት አይገኝም።

ሁለተኛ፣ በአሳብ ከልብ ፈጥሮ ደጉንና ክፉውን በምሳሌ በሚገልጽበት ጊዜ፣ ክፉውንና ደጉን የሚገልጡበትን ሰዎች አንባቢው በግብራቸው ባሕርያቸውን እንኳ ቢለይ፣ ደራሲው በ”ምሳሌ ስም” በአሳቡ የፈጠራቸውን ሰዎች “አቶ ክፉ ሰው”፣ “አቶ ደግ ሰው”፣ “ወይዘሮ ዓለሚቱ” ይህንንም በመሰለ ስም ይሰይማቸዋል። እንዲህ ያለው አካሔድ አብዛኛውን ጊዜ ችክ ይላል። ስለሆነም በደራሲዎችና በሕዝቡ ተለምዷል፤ ተወዷልም።

ፕሮፌሰር አፈወርቅ ከዚህ በላይ “ስለምን” እና “ምሳሌ ስም” ያልነውን አካሔድ በብዙው አይከተሉትም። በተከተሉበት ጊዜም፣ አንባቢው ሳይሰለች አሳባቸውን እንዲያስተውል አድርገዋል። ሙሉው ንግግራቸው ያማርኛን ባሕርይ እየተከተለ በረዘመበት ጊዜም ቢሆን፣ ግልጥና ያማረበት ነው። አንዳንድ ጊዜ ብቻ ቅጽል ሲያበዙ ነገሩ ጉት ይሆንባቸዋል። ፕሮፌሰር አፈወርቅ በደራሲነታቸው ሙቀት ያለበት ንግግር ማምጣት ዋና ባሕርያቸው ነው። ሙቀቱም የሚገባ ወይም ተሸጋጋሪ በመሆኑ፣ አንባቢው አሳባቸውንም በማይቀበልበት ጊዜ መሞቁ አይቀርም። በጽሑፍ ሥራቸው የሚያነሡት ሰው ወይም እንስሳ፣ ጫካ ወይም በረኻ ሁሉም ሕይወት ያለበት ሁኖ ይታያል።

ፕሮፌሰር አፈወርቅ “የአጤ ምኒልክ ታሪክ” እና አንድ ልብ ወለድ ታሪክ ጽፈዋል። የቀሩት በጣልያንና በፈረንሳይ ቋንቋ የጻፏቸው መጻሕፍት የአማርኛን ሰዋስውና የኢትዮጵያን ሁኔታ የሚያስታውቁ ናቸው።

afework-menelik

ፕሮፌሰር አፈወርቅ የአጤ ምኒልክን ታሪክ ሲጽፉ፣ ንጉሠ ነገሥቱ ከደረሰባቸውና ከሠሩት ዝርዝር ሳይገቡ ዋና ዋናውን ብቻ አመልክተዋል። ጥቂት ዝርዝር ያለበት፣ ስለ አጤ ምኒልክና የኢጣልያ መንግሥት መልእክተኞች የሚናገረው ክፍል ነው። የአጤ ምኒልክን ታሪክ ባጭሩ ካመለከቱ በኋላ የጣልያን መንግሥት መልእክተኞች ፕሮፌሰር አፈወርቅን እንዲረዷቸው በገንዘብ ሳይቀር ሊያባብልዋቸው እንደሞከሩ፣ እርሳቸው ግን ሳይታለሉላቸው በመቅረታቸው የንጉሣቸውን ፖለቲካ እንደደገፉ ለማስረዳት ይጣጣራሉ። በንግግራቸው ለምኒልከና ለሸዋ ሲሆን፣ ቁልምጫውንና ቃለ አጋኖውን ማብዛታቸው፣ ለሌላው ወረዳ ባላባትና ሕዝብ ሲሆን፣ ማዋረዳቸውና መሳቂያ ለማድረግ መታገላቸው፣ ለባለ ታሪክ የተገባውን እውነተኛ ሚዛን የያዙ በመሆን ፈንታ፣ ከዳተኛ ካለቻቸው አገራቸው ጋር ለመቃረብና የመንግሥቱን ሥራ የያዙትን ደስ ለማሰኘት የተነሡ ያስመስላቸዋል። ግን ደግሞ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ከባለ ታሪክ ልዩ ሥራ አንዳንዱን እንዳልዘነጉትና ለታሪክ ንግግር አዲስ መንገድ እንደ ጠረጉለት አጭሩ የምኒልክ ታሪክ እንደሚያስረዳ ማስታወቅ ይገባናል።

afework-tobya

“ልብ ወለድ ታሪክ” ለኢትዮጵያ የፈጠራ መጀመሪያ መጽሐፍዋ ነው። ከዚህ በፊት እንዳመለከትሁት ያገራችን ደራሲ አሳቡን በጽሕፈት ለመግለጥ ባሰበበት ጊዜ ባሳቡ የሚፈጥራቸው ሰዎች የግብራቸውን ስም የተጸውዖ ስም አድርጎ “አቶ መልካም ሰው”፣ “አቶ ክፉ ሰው” የሚሉትን አካሔድ ብቻ ይከታተል ነበር። የዛሬው ሰው የፕሮፌሰር አፈወርቅንና የኤውሮጳን መጻሕፍት በማንበቡ ልብ ወለድ ታሪክ ለመጻፍ ይጣጣራልና በር ከፋቹ ፕሮፌሰር አፈወርቅ በመሆናቸው ምስጋና ይገባቸዋል።

የፕሮፌሰር አፈወርቅ ልብ ወለድ ታሪክ የሚነግረን የሁለት ወጣቶችን ፍቅር ነው። ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሁነው፣ ሃይማኖታቸው የወንድየው እስላም የሴቲቱ ክርስቲያን ነው። ከሁለቱ በፍቅር ድል ሁኖ የወዳጁን ሃይማኖት የተቀበለ ወንድየው ነው። መጽሐፉ የፍቅር ኃይል ብርቱ መሆኑንና የንጹሕ ፍቅር አካሔድ እንዴት መሆን እንደሚገባው ይተርካል። እግረ መንገዱን ደግሞ፣ የዛሬ ሰባት ወይም ስምንት መቶ ዓመት በኢትዮጵያ ሲደረግ ከነበረው ሥራ ከብዙው ጥቂቱን ያመለክተናል።

ደራሲው የጽሕፈት አገላለጣቸው ደግ ሲሆን፣ ምክንያት ለመፍጠር ብዙ መንገድ አልተገለጠላቸውም። ባሳባቸው የፈጠሯቸው ሰዎች ለሚፈጽሙት ሁለት ሦስት ልዩ ልዩ ሥራ አንድ ምክንያት ሰጥተው፣ ያንኑ አንዱን ምክንያት ሳይለውጡ፣ ሁለት ሦስት ጊዜ ደጋግመውታል። ይህንና ሌላውን ያደራረግ ብልሐት (የቴክኒክ ጣጣ) የዋናው ሥራቸው ንድፍ ተስተካክሎ በመሔዱ አንባቢው እንደሌለ ይቆጥረዋል። ይህም አንድ ኪነ ጥበብ ነው።

ፕሮፌሰር አፈ ወርቅ ሁለት ሦስት ያህል ቲያትር ጽፈዋል። ነገር ግን እስካሁን ድረስ ሰው በቲያትር ጨዋታ አላያቸውም ደግሞም አልታተሙም።

እንደዚኸው ሁሉ ብዙ ደራስያን ጽፈው ያላሳተሙ አሉና ሥራቸው በሕዝብ ስላልታወቀ ስለነርሱ ለመጻፍ ከዚህ ሥፍራው አይደለምና እንተወዋለን። ቢሆንም ከነዚህ ያንዱን የበጅሮንድ ተክለ ሐዋርያትን ስም ማስታወስ የተገባ ነው።

፪ በጅሮንድ ተክለ ሐዋርያት ተክለ ማርያም

teklehawaryat-photo-2

አገራቸው ሸዋ፣ የተወለዱበት ዘመን ደግሞ 1875 ዓ.ም ግድም ነው። እርሻና የወታደርነት ሥራ በሞስኮብና በፈረንሳይ አገር ተምረው በኢትዮጵያ መንግሥት ከፍ ባለ ልዩ ልዩ ሹመት ላይ ኑረዋል። በመጨረሻ ጊዜም በፓሪስና በዤኔቭ የኢትዮጵያ መንግሥት ሚኒስትር ሁነው ነበር። ፍጹም አማርኛ በሆነ ግጥም ጥቂት ተረት ጽፈው ካሳተሙና በተረት ዓይነት ቲያትር ከጻፉ በኋላ፣ አሁንም ንጹሕ በሆነ አማርኛ ስለ እርሻ ትምህርት ጽፈዋል።

teklehawaryat-ershaበዚህም መጽሐፍ በአማርኛ ቃል ላልተገኘለት ለኬሚስትሪና ለሌላው ዕውቀት የተመረጠ ቃል በመገኘቱ ዕውቀትን በእውነት እጅ ካደረጉት ለደራሲ ቋንቋን እንደልቡ ማዘዝ እንደማያስቸግር ያስረዳል። በጅሮንድ ተክለ ሐዋርያት ለኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት መግለጫ የተናገሩትና የጻፉት ደግሞ የተሰወረን አሳብ ለመግለጥ ችሎታ እንዳላቸው ያስረዳል።

፫ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ

ነጋድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ

ነጋድራስ ገብረሕይወት ትውልዳቸው ትግሬ ሲሆን ከዛሬ 30 ዓመት በፊት ሙተዋል። በልጅነታቸው ነምሳ (ኦስትሪያ) አገር ብዙ ተቀምጠው በትምህርታቸው ተጠቅመዋል። ከጻፉት አብዛኛው ጠፍቶ በሕይወታቸው ሳሉ ስለ አጤ ምኒልክና የኢትዮጵያ ሕዝብ በኤርትራ ሲታተም ከነበረ ጋዜጣ አሳትመዋል። “የመንግሥትና የሕዝብ አስተዳደር” ብለው የሰየሙትን መጽሐፍ ከሞቱ በኋላ ወዳጆቻቸው አሳትመውታል።

በሁለቱም ሁሉ መጻሕፍት ኢትዮጵያዊ በሚረዳው አካሔድ የቤተ መንግሥቱ ሥራ ማሻሻል እንዳለበት ሰብከዋል። ሁለቱም መጻሕፍት ደራሲው በልበ ሙሉነት ስለሚገልጡት ከፍተኛ አሳብና ስለ ንግግራቸው ጥራት ምስክር ናቸው። በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ብዙ ጉዳይ ለማሠራትና፣ ለወደፊት ሕግንና ልማድን እያሻሻሉ ለማደስ ስላለብን ሥራ፣ ብርቱ አሳብ የሚያሳድሩ የሚያስፈጽሙም መጻሕፍት ናቸው።

(በክፍል አራት ይቀጥላል …)

2 thoughts on “የ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ደራሲዎች

    1. እባኮትን ከቻሉ፡ የ ነጋድራስ፡ ገብረህይወት፡ ባይከዳኝ፡ ታሪክ፡ ካሎት፡ ብናውቀው፡ በጣም፡ ጥሩ፡ ነው።

      Like

አስተያየት ለመስጠት

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s