የአስናቀች ወርቁ ኪነጥበባዊ ሕይወት
በኅሩይ አብዱ
“አስናቀችና ሙዚቃ”
ከቅጽበታዊው የተውኔት መድረክ ይበልጥ አብዛኞቻችን አስናቀችን የምናያይዛት ከክራሯና ከምታንጎራጉራቸው ዘፈኖቿ ጋር ነው። እንደ ኢየሩሳሌምን እንደምታስታውሱ ተስፋ አደርጋለሁ።
“እንደ ኢየሩሳሌም እንደ አኩስም ፅዮን ፣
ተሳልሜው መጣሁ አይንና ጥርሱን …”
የኢትዮጵክስ 16 – “The Lady With the Krar” – ሲዲ አስናቀች በ1966ና 1968 ዓ. ም. ያወጣቻቸውን ሸክላ ዘፈኖች የድምጽ ጥራት አሻሽሎ ለገበያ ቀርቧል። ኢትዮጲክስ 16 ሃያ ሁለት ዘፈኖችን አሰባስቧል፣ ዘፈኖቹ በሕዝባዊ ዜማዎች ላይ ተመስርተው ሰባቱ ግጥሞች በአስናቀች ሲደረሱ ሌሎቹ በጌታቸው ደባልቄ፣ አፈወርቅ ዮሐንስ፣ ተስፋዬ ለማና፣ ሸዋልዑል መንግስቱ የተገጠሙ ናቸው።
አስናቀች በክራር ራሷን አጅባ በምታንጎራጉራቸው ዘፈኖች የምታተኩረው ተቀጣጥሎ ያልተፋፋመ ወይንም የሰከነ ፍቅር ላይ ነው። ለአብነት ‘እንደ ኢየሩሳሌምን’ና ‘እሱ ርቆ ሄዶ’ን መመልከት ነው። የፍቅር ጉዞዋ በዘፈኖቿ ውስጥም ይታያል። የምታፈቅራቸው ሰዎች አያዛልቋትም፤ የሰው ሰው ሊሆኑ ይችላሉ ወይንም ስሜታቸው አብሯት አይፈካም። ለዚህም ነው ፍቅረኞቿን “ይፋ የማይወጣ ሰው”፣ “ፍቅር የማይገባው አጉል ሰው” እያለች የምትጠራቸው። አስናቀች ለወደደችው ፍቅሯን ከመግለጽ አትቆጠብም፣ ከመለማመጥም አትመለስም። አንዴ ፍቅሩ ከሰከነ ግን እርግፍ አድርጋ ትተዋለች። ሕይወቷም ዘፈኖቿም ምስክሮች ናቸው።
“መሞከር ይሻላል ሁሉንም መሞከር፣
ይፈጠር ይሆናል አንድ ደህና ነገር።”
መንገደኛው ልቤ 1966 ዓ. ም.
አስናቀች ወርቁ እነዚህን ስንኞች ስታንጎራጉር የሕይወቷን ሚስጥር የምታካፍለን ይመስላል። አስናቀች ዘወትር ሕይወቷን ወደ አዲስ መንገድ እንደመራችው ነው። ከልጅነት ወደ ትዳር፣ ከአንዱ ትዳር ወደ ሌላ፣ ያም ሲፈርስ ወደ አዲስ ፍቅረኛ፣ ከዛም ወደ ሌሎች ፍቅረኞች ተሻግራለች። ብዙ ነገር ሆናለች፤ ማንም ያልደፈረውን የሴት ተዋናይ፣ ከዛም አልፋ የሙዚቃ (ክራር) ተጨዋች ፣ ዘፋኝ (አንጎራጓሪ)፣ እንዲሁም የባሕልና የዘመናዊ ሙዚቃ ተወዛዋዥ፣ ሁሉንም ሆናለች።
“አስናቀችና ቴያትር”
አስናቀች “የፍቅር ጮራ” ተውኔት ውስጥ ከመሳተፏ በፊት የሴትን ገጸባህሪ የሚጫወቱት ወንዶች ነበሩ። የሚመረጡትም ጺም ገና ያላወጡ ፣ መልከ መልካም ወጣቶች – እንደ ተስፋዬ ሣህሉ (አባባ ተስፋዬ)፣ መርአዊ ስጦት፣ ተፈራ አቡነወልድ … የመሳሰሉት – ነበሩ። ምንም መልከ መልካም ቢሆን፣ ድምጽንም እንደፈለገ መቀያየር ቢችል፣ ወጣቱ አባባ ተስፋዬ (ወይንም ሌላ ወንድ ተዋናይ) የቧልት እንጂ ውስብስብ የሴት ገጸባህሪይ መጫወት የሚችል አይመስለኝም። በአስናቀች ፋና ወጊነት የሴቶችን ገጸባህሪ ሴቶች ራሳቸው ይጫወቱት ጀመረ፤ የሚሰሩትም ተውኔቶች ተአማኒነታቸው እየጨመረ ሄደ።
የዚህችን ሁለገብ ጠበብት ሕይወት የሚዳስስ መጽሐፍም በቅርቡ ታትሟል። አስናቀች መድረክ ላይ የምትጫወተውን የባለታሪክ ባህርይ ሙሉ በሙሉ እንደምትላበስ ደራሲው ይናገራል። ለምሳሌ የፍቅር ጮራ ላይ ከመድረክ ፍቅረኛዋ ጋር የነበራት ግንኙነት እውነተኛ በመምሰሉ ትርኢቱን የምትመለከተው የተዋናዩ ፍቅረኛ እያለቀሰች ዝግጅቱን አቋርጣ ወጥታለች (ገጽ 23)። በሌላ መድረክ ላይ “ሴተኛ አዳሪዋ” አስናቀች ኑሮዋን የመረጠችው እንደሌላው ስራ ዘመድ፣ ትምህርት ወይንም ጉቦ ስለማያስፈልገው እንደሆነ ትናገራለች። እውነታው የከነከናቸው የውቤ በረሃ ቆነጃጅት እንዲሁም ሌላው ተመልካች ገጸባህሪዋን (ወይንስ አስናቀችን?) በጭብጨባ ደግፈዋታል (ገጽ 36)።
አስናቀች ምን ያህል ተውኔቶች ውስጥ እንደተሳተፈች አላውቅም። መጽሐፉም አይናገርም። ደራሲው የፍቅር ጮራ ፣ እኔና ክፋቴ ፣ ዳዊትና ኦሪዮን ፣ ስነ ስቅለት ፣ ኦቴሎ ፣ እናት አለም ጠኑና ኤሪስ በጎንደር የተባሉትን ዘርዝሯል። የነዚህን ከአምስት እጥፍ በላይ እንደሰራች አልጠራጠርም። ነገር ግን ተጽፎ ካልተቀመጠ ይረሳልና፣ ደራሲው የወደፊት እትም ላይ ቦታ ቢሰጠው መጽሐፉን ያሳድገዋል። ገጣሚውና ጸሐፌ ተውኔቱ ጸጋዬ ገብረ መድህን በበልግ መጽሐፉ ፣ “በመስከረም 19 ቀን 1954 ዓ. ም. ዓርብ ማታ በተከፈተ (የበልግ ተውኔት) ጊዜ፣ … ጌታቸው ደባልቄ እንደ ወፈፌው ሰዓሊ እንደ ኅሩይ፣ … አስናቀች ወርቁ እንደ ብኩኗ ቆንጆ እንደ ጽዮን ሆነው ተጫውተው ነበር” በማለት ዘግቧል። በተጨማሪም አውራስ መጽሔት 1985 ዓ.ም. ቁጥር 1 ላይ እንዳየሁትም “ደመ መራራ”ና “ዋናው ተቆጣጣሪ” የተባሉ ተውኔቶች ውስጥ ተሳትፋለች።
“መጽሐፉ”
የአስናቀች ትዝታዎቹን በጽሑፍ አዘጋጅቶ ያቀረበልን ጌታቸው ደባልቄ ነው። ጌታቸው ላለፉት 50 አመታት ከዘመናዊ የኢትዮጵያ ቴያትር አብሮ ድኾ፣ አድጎ፣ ጎልምሷል – እንደ ተዋናይ፣ አዘጋጅ፣ ደራሲ እንዲሁም አስተዳዳሪ። በተጨማሪም ጌታቸው ስለ ዘመናዊው የኢትዮጵያ ሙዚቃና ቴያትር አጀማመርና ሂደት ማወቅ ለፈለጉ የመረጃ ምንጭ ኧረ ወንዝም ነው። የሰበሰባቸው ፎቶዎችና ሰነዶች፣ እንዲሁም ለጠየቁት በደስታ የሚያወጋቸው ትዝታዎቹ፣ ከመጽሔቶች ተርፈው ሙሴ ፋልሴቶ አዘጋጅቶ የሚያቀርባቸውን የኢትዮጲክስ (Ethiopiques) ሲዲዎች እያጀቡ ነው።
ደራሲው ከባለታሪኳ ጋር የተዋወቀው በ1945 ዓ.ም. ነበር። ጌታቸውም እንደሚለው፣ “ስለሷ ሕይወት መጠነኛ ታሪክ ለማስቀረት ምኞት ካደረብኝ ቆይቷል” ለምንስ መጽሐፉን ጻፈ? “… ለነገዎቹ የኪነጥበብ ሰዎችና ታሪክ ጸሐፊዎች” ለማስተላለፍ ይመስላል።
መጽሐፉ አራት ክፍሎች አሉት፤ እነሱም ልደትና እድገት – ውስብስብ ሕይወት ፣ የጥበብ ጮራ ፣ ከጠባቡ ወደ ሰፊው የኪነጥበብ አለምና፣ ጡረታና ትዝታ ናቸው። አባቷን የማታውቅ፣ እናቷም በሕጻንነቷ የሞቱባት አስናቀች፣ ልጅነቷን ያሳለፈችው አንዱ ዘመድ ወደ ሌላው እየተቀባበላት ነበር። በብቸኛው የአዲስ አበባ የሴቶች ት/ቤት የመማር እድሏን ስለተነፈገች፣ ምርጫ ሆኖ የታየው ለትዳር መዘጋጀት ብቻ ነበር። አክስቷም ጣሊያን አገር ሚስትና ልጆቹን ላስቀመጠው ለአንዱ ዳሯት። ልጅነቷን ያልጠገበችው አስናቀች ግን የትዳር ማተብ ሊያስራት እንዳልቻለ በመጀመሪያው ክፍል እናያለን።
ሁለተኛው ክፍል የዘመናዊን ቴያትር አጀማመር በትንሹ ዳስሶ አስናቀችም በምን መልክ “የፍቅር ጮራ” ተውኔት ላይ የመጀመሪያዋ የሴት ተዋናይት እንደሆነች ይተርካል። የሚቀጥለው ክፍል የአስናቀችን በ“ዳዊትና ኦሪዮን” (ለአፄ ኃይለ ሥላሴ የብር ኢዮቤልዮ የተዘጋጀ ተውኔት) የተዋጣለት ትወና፣ እንዲሁም ከክራሯ ጋር የመሰረተችውን ፍቅር አጀማመር ያወሳል። የመጨረሻው ላይ ክፍል ከጡረታ ይልቅ ሁሌ የሚፋጀው የአስናቀች ፍቅር ላይ ያተኩራል፤ የፍቅር ሕይወቷ ለብቻው አንድ ተውኔት ሳይወጣው አይቀርም። በኢትዮጲክስ አዘጋጅ ከቀረበው አጭር የሕይወት ታሪክ በኋላም መጽሐፉ በሁለት የታወቁ የአስናቀች የዘፈን ግጥሞች ይደመደማል።
የሽፋኑም ምስሎች ፣ የደራሲውንም ጉርድ ፎቶ ጨምረን መጽሐፉ ከሃያ በሚበልጡ ፎቶዎች አሸብርቋል። የናንተን ባላውቅም እኔ በበኩሌ ፎቶ ወይንም ምስሎች የተነሰነሱበት መጽሐፍ ይስበኛል። ምስሎች ከታሪክ ጋር በአግባቡ ሲዋሀዱ ጽሑፍን ያጣፍጣሉ፤ ምናባችንንም “በፈረሱም ይኸው ሜዳውም ይኸው” እያሉ ያደፋፍራሉ። አዘወትረን በሀገራችን መጽሐፎች እንደምናየው ፎቶዎቹ ደብዝዘው ሰው ከሰው የማይለይበት ደረጃ አልደረሱም። እነዚህዎቹ ጥርት ብለው ወጥተዋል ፤ ደራሲውና አሳታሚው ምስሎቹን ታሪካዊነት ፋይዳ ስለሰጡ ፎቶዎቹን ከደህና ምንጭ ቀድተው ለፎቶ በሚስማማ ወረቀት አሳትመዋል።
የፊት ሽፋኑን ፎቶ ብትመልከቱት፤ ለብቻው ስንት ታሪክ ይናገራል! መቸስ አስናቀች ባሕላዊነትን ከዘመናዊነት ጋር ያለ ግጭት ካዋሐዱ ጥቂቶች አንዷ መሆን አለባት። የእድሜ ባለፀጋዋ ወጣትነት ከልብ ትኩሳት እንጂ ከቁጥር ማነስ እንደማይገኝ የምታምን ትመስላለች፤ ወይንስ ትዝታዋን የሙጥኝ መያዟ ነው? የአይኖቿ ከኛ መደበቅስ? ብዙ ሚስጥር በሆዷ ይዛ ነውን? እኛን አፍራ ሳይሆን ሸክሙ እንዳይከብደን ያዘነች ትመስላለች። ይሄ በሙላ ከአንድ ፎቶ!
ፎቶዎቹ ሌላም ብዙ ታሪክ ያወሳሉ። አስናቀች የመጀመሪያዋ የሴት ተዋናይ ከመሆኗ በፊት የሴትን ገጸባህሪ ማን ይጫወት ነበር? ገጽ 19 ያለውን ፎቶ ይመልከቱ። በ1945 ዓ. ም. ሁለተኛ ማዕረግ ተቀምጦ ቴያትር ለመመልከት ስንት ብር ያስፈልግ ነበር? ምን ያህልስ የተውኔት ማስተዋወቂያ ይታተም ነበር? መልሱን ገጽ 21 ያገኙታል። ሞኝና ወረቀት … ልበል መሰለኝ።
ጌታቸው ደባልቄ በዚህ አነስተኛ መጽሐፍ ስለሚወዳት ጓደኛው ያሉትን ትውስታዎች አስተላልፎልናል። በተጨማሪም ስለ ቴያትርና ሙዚቃ አጀማመር፣ ወጣቷንም አዲስ አበባን ለመተዋወቅ ለሚፈልጉ ጥሩ እይታ ይሰጣል። ይህን መጽሐፍ እንደተለመዱት በዓመተ ምህረትና በመረጃዎች እንደተሞሉ የሕይወት ስራዎች አላየሁትም። ከዚያ ይልቅ በትውስታ/ትዝታ ዘርፍ ቢመደብ አንባቢውንም አያደናግርም።
ምን ይጨመር? ምንስ ይቀነስ? አስናቀች የተሳተፈችባቸውን ተውኔቶች፣ የዘፈነችባቸውን የሙዚቃ ሸክላዎች ቢዘረዘሩ የበለጠ የምናውቃት ይመስለኛል። የመጽሐፉ መጀመሪያና አራተኛው ክፍል በባለታሪኳ ድምጽ ቢተረክ ቋንቋዋም ስሜቷም የሚዋሐደን ይመስለኛል። መጽሐፉ በመታተሙ እጅግ ተደስቻለሁ፤ በሕይወት ያሉ ኢትዮጵያውያን ብዙ ጊዜ መጽሐፍ አይጻፍላቸውምና!
እንደ መጽሐፉ መዝጊያ ዓረፍተ ነገሮች …
“ይህ የኔ ጽሑፍ ለመጭዎች ጸሐፊዎች መግቢያ በር ይሆናል። ሊያባዙት ሊያሳጥሩት ቀና መንገድ ይሆናል። በበኩሌ የዘለልኩትን ዘልዬ ያሳጠርኩትን አሳጥሬ በዚህ ሁኔታ ደምድሜዋለሁ።”
My only in depth reading is on the biography of Asnaqech. Loved and posted on my Facebook wall.
Will pay more attention henceforth.
LikeLike
Des yilal
LikeLike
ጠሊቅ መጣጥፍ! ደስ ፈቅ አርጎኛል!
LikeLike