አድዋ
፩
ኮንት አንቶኔሊ የውጫሌ ውል እንዳልሆነለት አይቶ በንዴት ያን የታተመውን ደብዳቤ ብጭቅጭቅ አርጎ ቀዳዶ ጣለና “እንግዲህ ፍቅራችን ፈረሰ” ብሎ የጦርነቱን ነገር ገልጦ ተናግሮ ወጣ።
እቴጌ ጣይቱ ከትከት ብለው ስቀው “የዛሬም ሳምንት አድርገው በዚህ የሚደነግጥልህ የለም። ሂድ የፈከርህበትን አድርግ እኛም የመጣውን እናነሣዋለን። እግሩን ለጠጠር፣ ደረቱን ለጦር ሰጥቶ አገሩን የማያድን ሰው ከዚህ ያለ አይምሰልህ” አሉት።
ያው ፈረንጅ በንዴት እጅና እግሩ እየተንቀጠቀጠ ፊቱ ጭው ብሎ እንዶድ የጨረሱበት ሸማ መስሎ እጅ ሳይነሳ ተወርውሮ ወጣ።
ዳግማዊ ምኒልክ እንግዴህ ከኢጣልያ ጋር በመዋጋታቸው ቁርጥ አደረጉና መሳሪያ እያሰናዱ ተቀመጡ … አጤ ምኒልክ ጭራሽም ሳይታረቁ፣ ጭራሽም ሳይጣሉ ዝም ብለው ነፍጡን፣ ጥይቱን፣ መድፉን ከአውሮፓ እያስጓዙ ለመሰብሰብ አልቦዘኑም ነበረ።
ለኢጣልያም “ፍቅር ከወደዳችሁ አንድ አራት ሚሊዮን የሰናድር ጥይት ስደዱልኝ” ብለው ላኩ። የኢጣልያ መንግሥት ግን ነገሩን አዙሮ ሳያይ እሺ ብሎ አራት ሚሊዮን ጥይት ሰደደ።
አጤ ምኒልክ በዚህ ሞኝነት እየሳቁ ነገራቸውን ሁሉ እያበጃጁ እያሰናዱ “ተጋፍቶ ቢመጣም እንገጥመዋለን፤ ተጋፍቶም ባይመጣ የያዘውን አገር እናስለቅቃለን” ይሉ ጀመር።
“ዳግማዊ አጤ ምኒልክ” 1901 ዓ.ም፤ ገጽ 78-85
፪
ጣይቱ ፡ “አይዞሽ ማሚትዬ! … አይዞሽ የኛው መድፍ ነው”
ዘውዲቱ ፡ “ፈጣሪ በመንበሩ እያለ፣ እውነት የአገራችንን ክፉ ጨክኖ ያሳያን ይሆን እናቴ?!”
ጣይቱ ፡ “አይዞሽ ማሚትዬ! አይዞሽ! በዚህ እድሜሽ፣ ከእልፍኝ ይልቅ ጦር ሜዳ መገኘትሽ …
እንዲህ በአንቺ እድሜ ግድም እያለሁ፣ የአጼ ቴዎድሮስ እስረኛ ሆኜ፣ ከቴዎድሮስ የተማርሁትን አጫውቼሽ የለ?
ዘውዲቱ ፡ “አዎን ነግረውኛል። አባቴም አልፎ አልፎ ስለአጼ ቴዎድሮስ የሚነግሩኝ ከልቤ እንደተጣፈ ነው”
ጣይቱ ፡ “አዎን … ምንም ልጅ ሆነው በምርኮ ቢሄዱ፣ አባትሽ፣ እንደልጅ የሚያይዋቸውን ቴዎድሮስ፣ እንደአባታቸው ቆጥረው ብዙ ነገር ቀስመዋል … አየሽ ማሚትዬ የነገን ሸክም በጽናት የሚቀበለው ዛሬ ያዘጋጁት ልብና ዛሬ ያነጹት መንፈስ ነው …
በሉ ተነሱ ግስሎቼ! … ተነሱ አንበሶቼ! … አገራችሁ በናንተ ተከብራ፣ እኔን እናታችሁንም በእናንተ በልጆቼ ለመኩራት ያብቃኝ … ሂዱ! ኩራቶቼ! ሂዱ ጌጦቼ! … እሰይ አንበሶቼ! እሰይ! … እሰይ ግስሎቼ! እሰይ! … እሰይ ጀግኖቼ! … እሰይ!
“እቴጌ ጣይቱ – ታሪካዊ ተውኔት” 2000 ዓ.ም፣ ገጽ 93-99።