የፒያሳው ኬዎርኮፍ ህንጻ
(ክፍል 2)
በሕይወት ከተማ
(… ከክፍል አንድ የቀጠለ)
በ1900ዎቹ መጨረሻ ማቲክ ኬዎርኮፍ በተባለ ነጋዴ ለሱቅነት የተገነባው ሕንጻ ለሃያ አመታት ያህል በዚሁ በመደብርነቱ ሲያገለግል ቆየ። ከስድስቱ የሕንጻ ክፍሎችም ሁለቱ (የዛሬዎቹ “ካስቴሊ” እና “አንበሳ ባንክ”) በዛን ዘመን የሕንጻው አካል አልነበሩም። ከ1928 ዓ.ም በኋላ ግን ይህ ታሪከኛ ሕንጻ ብዙ መሰናክል አጋጠመው። ሆኖም፣ ሕንጻውም በበኩሉ በርካታ አይነት ለውጦችን በማድረግ ከዘመኑ ጋር ለመሄድ ጥሯል።
Casa Littoria (1928-1933 ዓ.ም.)
በሚያዝያ 1928 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ (ቀዳማዊ ኀይለሥላሴ በባቡር ሲሰደዱና ጣልያን ገስግሶ መዲናችን ሲገባ) የአዲስ አበባ ሕዝብ አራዳን መዝረፍ እና ማውደም ጀመረ። በሚቀጥሉት አራት ቀናት ውስጥ ብዙ ንብረት ጠፋ፤ እጅግ ብዙ ሱቆች፣ ሆቴሎችና ንግድ ቤቶችም ተቃጠሉ። የኬዎርኮፍ ሱቅም ይህ እጣ አልቀረለትምና ከአካባቢው ሕንጻዎች ጋር ተቃጥሎ በአጥንቱ ቀረ።

ጣልያንም ወደ አዲስ አበባ ከገባ በኋላ የሕንጻ ባለሙያዎቹ የኬዎርኮፍን ሕንጻ ውበት ለማየት አልተቸገሩም። አፍርሰው በሌላ በመተካት ፋንታ እንዳለ ለማደስ ወሰኑ። አንዳንድ ለውጦችን ግን ማድረጋቸው አልቀረም።


ከጎን በምስሉ እንደሚታየው ፣ ዋነኛው ለውጥ “ሕ4” እና “ሕ5” ከህንጻው ጋር መቀላቀላቸው ነው። የሕንጻው አካል ለማድረግ የተጠቀሙበትም ዋነኛው መንገድ በቀኝ በኩል ላለው “ሕ5” (የዛሬው ካስቴሊ) የላይኛውን ፎቅ መስኮቶች ቅስት ማድረግ ነበር። በተጨማሪም ቀድሞ በ”ሕ1” እና “ሕ3” አናት እና ወገብ ላይ የነበረውን ተደራራቢ መስመር ወደ “ሕ5” እንዲቀጥል አደረጉ።

በግራ በኩል ላለው “ሕ4” ግን እምብዛም ለማመሳሰል ጥረት የተደረገ አይመስልም። የውስጡ ፕላን እንዲገናኝና እንደ አንድ ወጥ ሕንጻ እንዲዋሐዱ ቢደረግም፣ ለአይን ግን እስካሁን ልዩነታቸው ጎልቶ ይታያል። “ሕ4” የሌላውን ሕንጻ ክፍሎች ዋነኛ ጸባይ (ከጥርብ ድንጋይ መሠራቱን) እንኳን አላሟላም።
በተጨማሪም፣ (ከእድሳት በኋላ) ጣራው ተነስቶ ወደውጭ ወጣ ብሎ የነበረው ገባ ተደርጎ የጣራው ተዳፋት በጣም አጭር ሆነ። እንዲሁም፣ የጣራው ቆርቆሮ እንዳይታይ ግድግዳው በትንሹ ወደላይ ከፍ ብሎ እንዲቀጥል ተደረገ።
የላይኛዋም ህንጣ (“ሕ6”) ከስሯ ጓደኛ ተፈጥሮላት አዲሲቷ እንጎቻ የራሷ ጣራና ትንንሽ መስኮቶች እንዲኖራት ተደረገ። የቀድሞዋ እንጎቻም ወደላይ ከፍ ብላ በአምስት ማእዘን ጎኖቿ ላይ የራሷ ቅስት መስኮቶች ተሰሩላት።


እነዛ ትናንሽ አራት ማዕዘን መስኮቶችም ተደፍነው በግራ በኩል (“ሕ2” ክፍል) ያሉት በርና መስኮት ሁለቱም ዝቅ ብለው እንዲታዩ ተደረገ። በቀኝ በኩል (“ሕ3” ክፍል) ደግሞ አንደኛው መስኮት ከፍ ብሎ ከ“ሕ1” ጋር ሲቀላቀል፣ በሩ ግን ዝቅ እንዳለ በተዛነፈ ዲዛይን ተሠራ።(ምስል 21 – የመስኮቶች አቀማመጥ ከእድሳት በኋላ)
በመጨረሻም፣ መስኮቶቹ በሙሉ ያራት ማዕዘን ጠርዝ ባላቸው መስታወቶች ተቀይረው ከፎቁ ላይ “Casa Littoria” የሚል ጽሑፍ ካናቱ በትልቁ ተቀመጠበት። ህንጻውም በዚህ አዲሱ የፋሽስት ኢጣልያ አስተዳደር ቢሮነቱ ከ”ፒያሳ ሊቶሪዮ” አደባባይ ፊት ደረቱን ነፍቶ ቆሞ ካራት አመት በላይ አገለገለ።

የኢትዮጵያ የርሻ ባንክ (1930ዎቹ-1960ዎቹ)
ምንም እንኳን ጣልያን ወጥቶ ነፃነት ቢመለስም፣ ህንጻው ወደ ቀድሞው ባለቤት ወደ ኬዎርኮፍ ቤተሰቦች የተመለሰ አይመስልም። በኒህም ዓመታት፣ ለተለያዩ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች (እርሻ ባንክ፣ ንግድ ምክር ቤት) በቢሮነት ማገልገል ጀመረ።

በ1950ዎቹ አካባቢ አሁንም አነስ ያለ እድሳት ተደረገበት። ይህም የሚታየው በተለይ ከላይኛዋ እንጎቻ ህንጣ ላይ ነው። አምስት ማዕዘኗ በጎባጣ መስኮቶች ፋንታ በአራት ማዕዘን መስኮቶች ተተኩ። ሶስቱ መግቢያ በሮችም የበር ፍሬም ለውጦች ተደርገውባቸዋል።



ከኤልያስ ሆቴል እስከ ሮያል ኮሌጅ (1970ዎቹ-2000ዎቹ)


ከ1960ዎቹ በኋላ የተደረገው ዋነኛ ለውጥ “ሕ1” መሀል ላይ የነበሩት ሶስት ዋና መግቢያ በሮች ወደ ሁለት መስኮትና አንድ በር መቀየራቸው ነው። ይህንንም ለማድረግ ባለሙያዎች ከቀድሞው ሦስት በሮች ግራና ቀኝ የነበሩትን መስኮቶች አስመስለው በር 1 እና 3 ግርጌ የመስኮት ድጋፍና ጌጥ ከተመሳሳይ ድንጋይ አበጅተዋል።

በተጨማሪም፣ የ”ሕ1” አንዱን መስኮት (በግራ ያለውን) ወደ በር ለመቀየር ተወስኗል። ይህንንም ለማድረግ የቀድሞውን መስኮት ታችኛ ድጋፍ እና ጌጥ ጥርብ ድንጋዮች ሙሉ በሙሉ ነቅለው (ቆርጠው) ለማውጣት ተገደዋል። ከዚህም ሂደት የተረፈው የአሁኑ በር ጠርዝ በሊሾ ሲሚንቶ ለማስተካከል ሞክረዋል።
በህንጻው ሁለተኛ ፎቅ ወደ ባንኮኒ ያስወጡ የነበሩት ሰባት በሮች ከአንዱ በስተቀር (በቀኝ በኩል መጨረሻ ያለው) ሁሉም ወደ መስኮትነት ተቀይረዋል። የላይኛውም ህንጣ (“ሕ6”) እንደገና ሌላ እድሳት ተደርጎበት የመስኮቱ ማዕዘን በመጠኑ ሰፍቷል።

በተጨማሪ ግን፣ ከግልጋሎትና አንዳንድ የቀለም ለውጥ ውጭ እምብዛም ለውጥ አይታይም። ከመጠቀም ብዛትና ከጥገና እጦትም እንደ ብዙዎቹ የሀገራችን ታሪካዊ ሕንጻዎች ጃጅቶ ይታያል።
በአሁኑ ጊዜ ይህ ህንጻ በቅርስነት ተመዝግቧል። በአሁኑም ይዞታው ህንጻው ሮያል ኮሌጅን፣ አቢሲኒያ ባንክን እና ካስቴሊ ሬስቶራንትን በውስጡ ያስተናግዳል። የካስቴሊ ቤተሰብ በጣልያን ወረራ ጊዜ በ1928 ዓ.ም. አዲስ አበባ እንደገቡ ይነገራል። ኋላም ጣልያን ካገር ሲወጣ አዲስ አበባ ቀርተው በ1940ዎቹ መጨረሻ ካስቴሊ ምግብ ቤትን ከፈቱ። ታዲያ ይህ ምግብ ቤት በምርጥ የጣልያን ምግብ አዘገጃጀቱ የአለም አቀፍ ተወዳጅነት አትርፏል። ብራድ ፒት እና ጂሚ ካርተርም ሳይቀሩ ስፓጌቲያቸውን በዚሁ ምግብ ቤት እንደጠቀለሉ ይወራል!
የኬዎርኮፍ ኪነ–ህንጻ ስልቶች

በመጀመሪያው የአሰራሩ ውጥን ብናየው የህንጻው ስልት (Architectural Style) በአጠቃላይ “እንዲህ ነው” ብሎ ለመፈረጅ ያስቸግራል። ነገር ግን ለያይተን ብንመለከት፤ (ሀ) ድርድር ቅስት መስኮቶች (Arched Windows)፣ (ለ) የጣራ ክፈፍ ስር ያለው ጌጥ (Entablature)፣ (ሐ) የህንጻው ወገብ እና ግርጌ ላይ የሚዞሩት ተደራራቢ መስመሮች (Stone Bands)፣ (መ) ቋሚ-መሳይ አምዶች (False Columns)፣ (ሠ) ሙሉ የጥርብ ድንጋይ ህንጻ ስራ፣ (ረ) ወጣ ገባ ማዕዘን ስራ (Quoins)፣ እንዲሁም (ሰ) የባንኮኒው አጋጌጥ መንገድ በአውሮፓ ከ1832-1911 በሰፊው ይሰራበት የነበረውን “Renaissance Revival” የተሰኘውን የሥነ ህንጻ ስልት ያስታውሰናል።
በተመሳሳይ መልኩ ደግሞ፤ (ሸ) የጣራው ክፈፍ ወጣ ብሎ አሰራር፣ (ቀ) የጣራው ተዳፋት ስፋት፣ (በ) የመስታዎቶቹ ፍሬም አሰራር፣ (ተ) የጣራው ክፈፍ ጌጥና ጉልላት (Fascia Board Ornamentation) (ቸ) የጣራ ስር ፎቅ (Dormer Floor)፣ እና (ኀ) ከአናት ያለችው ህንጣ አሰራር፤ የ “እስያ” የሥነ ህንጻ ጥበብ እና በተለይም ከ1829–1893 በአውሮፓ የነበረውን እስያ-ገረፉን “Victorian Architecture” ያስታውሰናል።
በአጭሩ ኬዎርኮፍ ህንጻ የተለያዩ የኪነ-ህንጻ ስልቶችን ያንጸባርቃል::
በጣልያን እድሳት ጊዜ ብዙዎቹን የ “Victorian Architecture” የሚያሳዩትን ስልቶች አስወግዶ ወደ “Renaissance Revival” እንዲጠጋ ያደረገው ይመስላል። ማለትም (1) የጣራውን ክፈፍ ማስወገድ፣ (2) የጣራውን ተዳፋት አጭር አድርጎ ግድግዳውን ወደላይ በመቀጠል እንዳይታይ ማድረግ (3) የመስታወቶቹን ፍሬሞች በሙሉ በአራት መዓዘን መቀየር፣ (4) የጣራ ስር ፎቅን (Dormer Floor) ማስወገድ፤ ወደዚህ ስልት እንዲጠጋ ያደርገዋል። አሁንም ግን ሙሉ ለሙሉ ይህን የኪነ-ህንጻ ስልት ይከተላል ለማለት ያስቸግራል። በተጨማሪም ጣልያን ከህንጻው ፕላን ጋር ካቀላቀላቸው ህንጻዎች መካከል “ሕ4” ከጠቅላላው ስልት ጋር እንዲጣረስ አድርጎታል።
በአሁኑ ይዞታው ከጣልያን እድሳት እምብዛም የተለወጠ ነገር ባይኖርም፣ አንዳንድ በግዴለሽነት እንዲሁም ለግልጋሎት መመቸት ተብለው የተቀየሩ ነገሮች ከአጠቃላይ የህንጻው ቢጋር ጋር የማይሄዱ ሆነው እናገኛቸዋለን።
ለምሳሌ፣ አናት ላይ ያለችው እንጎቻ ህንጣ ከጎባጣ መስኮቶች ወደ አራት መአዘን መቀየሯ ከየትኛውም የህንጻው ቢጋር ጋር አይሄድም። እንዲሁም የግራና የቀኙ “ሕ2” እና “ሕ3” አለመመሳሰል የህንጻውን ሚዛናዊ እይታ ያዛባዋል። ወደ ባንኮኒው የሚያስወጡት በሮችም ወደ መስኮት መቀየር ባንኮኒውን ጥቅም ያሳጡታል።
በአጠቃላይ ይህ የመቶ አመት እድሜ ጠገብ ህንጻ ሂደታዊ ለውጥ ከሌሎች የአዲስ አበባ ህንጻዎች በልዩ መልኩ የሚታይ አይደለም። ማንኛውም ህንጻ ሕይወት ያለው ፍጡር ይመስል ያድጋል፣ ይጎረምሳል፣ ያረጃል፣ ይታደሳል፣ ይሞታል። የመዲናችንን ህንጻዎች በተመሳሳይ መልክ በቅርበት ብናስተውላቸው ተዘርዝሮ የማያልቅ የከተማችንን ታሪክ መልሰው ያንጸባርቁልናል።
ዋው! በጣም ደስ የሚል ነው በእውነቱ የህንጻው ስያሜ ምን እንደሚባል ባላውቅም በ2000ዎቹ ውስጥ በሮያል ኮሌጅ ውስጥ ተምርያለሁ። ግን የህንጻው ጥበብ ደስ ይላል።
LikeLike
Dear Hiwot,
You are onto something consequential. I can see the hard work that went into putting together this piece of history. Thanks. I am also wondering if there are plans to extend the same treatment to cities such as Jimma, Diree Dawa, aso.
LikeLike
It is one of those rare essays on the architecture of Addis Ababa. I am wondering why I have not yet known you. We gotta read more of your writings. God bless.
LikeLike