የፒያሳው ኬዎርኮፍ ሕንጻ
(ክፍል 3)
በሕይወት ከተማ
(… ከክፍል ሁለት የቀጠለ)
አራዳ የመዲናችን ንግድ ማዕከል በነበረችበት ዘመን ትላልቆቹን ሱቆች የሚያስተዳድሩት የውጭ ዜጎች (ግሪኮች፣ አረቦች፣ አርመኖችና ህንዶች) ነበሩ። ከነዚህም የናጠጡ ነጋዴዎች መካከል አርመናዊው Matig Kevorkoff (እንዳገሬው አጠራር ማቲክ ኬዎርኮፍ) አንዱ ነበር።
ጥቂት ስለ ማቲክ ኬዎርኮፍ
ኬዎርኮፍ በ1859 ዓም ኢስታምቡል ውስጥ ተወለደ። በቆንስጣንጢኖስም (Constantinople) በአርመን ትምህርት ቤት ተምሮ ወደ ግብጽ ተጓዘ። ለአጭር ጊዜ ግብጽ ውስጥ ቆይቶ በ1888 (በአድዋ ድል ወቅት) ወደ ጅቡቲ አመራ። በጅቡቲም ቆይታው የፈረንሳይኛ ተናጋሪ እና የፈረንሳይም ዜጋ ለመሆን በቃ።

ኬዎርኮፍም ከአጎቱ ጋር በመሆን ከጅቡቲ ትንባሆ ወደ ፈረሳይ ሐገር በመላክ ትልቅ ንግድ ጀመሩ። ቀስ እያለም ንግዱን ወደ ሐረር፣ ድሬዳዋ፣ እና አዲስ አበባ አስፋፋ። ጎራዴ፣ ሰይፍ፣ ጩቤ እና የመሳሰሉትን በ1890ዎቹ በሐረር ያመርት እንደነበር አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ጥይትና መሳሪያም በማስመጣት በአዲስ አበባ ሱቁ ይሸጥ እንደነበር የቀድሞ ደብዳቤዎች ያሳያሉ፤
“ይድረስ ከነጋድራስ ይገዙ – ማቲክ ጊዎርኮፍ መቶ ሳጥን የፉዚግራ ጥይት ከድሬዳዋ ወደ አዲስ አበባ አምቷልና እንዳይከለከል ይሁን።”
[ግንቦት 4 ቀን 1899 ዓ.ም. አዲስ አበባ]
በጣልያን ወራራ ዋዜማ ግንቦት 29, 1927 ዓ.ም. የወጣው ብርሃንና ሰላም ጋዜጣም ይህንንኑ ይጠቁማል።

የትንባሆ ንግድ በጣም አዋጪ ሆኖም ስላገኘው በአዲስ አበባ የትንባሆ ብቸኛ አስመጪ ሞኖፖል ይዞ ንግዱን በሰፊው ተያያዘው። በመጋቢት 1921 ዓ.ም. አእምሮ ጋዜጣ ስለ አገሪቱ የትንባሆ ሞኖፕል ለተጻፈበት ትችት መልስ ሲሰጥም እዚህ ይነበባል።
ከዚህም በተጨማሪ ጥጥ፣ ሐር፣ መጠጥ፣ ዘይት፣ ሳሙና፣ የህንጻ መሳሪያዎች፣ ብትን ጨርቅ፣ ስጋጃ፣ ሰዓት እና የመሳሰሉትን አስመጭና ላኪ ሆኖ ይሰራ ነበር።



እንዲሁም ኬዎርኮፍ የኮኛክና የተለያዩ መጠጦች ዋነኛ አስመጪ እንደነበር ምንጮች ያሳያሉ።
“መገን ያራዳ ልጅ ጠመንጃም የላቸው፤
በየደረሱበት ብርጭቆ ግምባቸው።
… ውስኪና ኮኛኩ ሲረጭ እንደውሃ፤
እንዴት ነሽ አራዳ የውቤ በረሃ።”
ለዚህ ሁሉ የንግድ ሥራው ይሆን ዘንድ ነበር በአራዳ የሚገኘውን ኬዎርኮፍ ህንጻ ያሰራው። ይህም የኬዎርኮፍ ሕንጻ የትምባሆ ሞኖፖል (“Tobacco Regie”) ዋና ቢሮ ሆኖ አገልግሏል። (ሕንጻው በአሁኑ ጊዜ “ሮያል ኮሌጅ”፣ “አቢሲኒያ ባንክ” ፣ “ካስቴሊ ሬስቶራንት” እና ሁለት ቡቲኮችን በመያዝ እያገለገለ ነው።)

የኬዎርኮፍ ህንጻ ከመሰራቱ በፊት ኬዎርኮፍ አራዳ ውስጥ በሁለት ሌሎች ሱቆች ውስጥ ንግዱን ያካሂድ እንደነበር ምንጮች ያሳያሉ። ከደጎል አደባባይ ፊት ለፊት ከአያሌው ሙዚቃ ቤት በስተቀኝ በነበረ (አሁን የፈረሰ) ጥንታዊ ህንጻ ውስጥ ኬዎርኮፍ ሱቅ እንደነበረው ይታያል።

ከዚህም በተጨማሪ እስከ 1920ቹ የፖስታ ቴሌግራፍና ቴሌፎን ህንጻ የነበረው (የአሁኑ “ሲኒማ ኢትዮጵያ” እና “ትራያኖን ካፌ”) በ1900ዎቹ ዓ.ም. መጀመሪያ የኮዎርኮፍ ሱቅ እንደነበረ ይታያል።

ኬዎርኮፍ ከዚህም ሌላ የሚታወቀው በፈረንሳይ ሌጌሲዎን ውስጥ የዲፕሎማሲና የማስተርጎም ስራዎችን በመሥራት ነበር። ከአንደኛው አለም ጦርነት በኋላም የትውልድ ሃገሩ አርሜንያ ስትመሰረት ብዙ የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል። በ1911 ዓ.ም. ከጓደኞቹ ጋር በመሆን 1000 የእንግሊዝ ባውንድ አዋጥተው ለአዲሲቷ አርሜንያ አውሮፕላን አበርክተው ነበር። በ1911 ዓ.ም. ደግሞ ለአርሜኒያ በኢትዮጵያ ተወካይ (እንደ አምባሳደር) ሆኖ ተመርጦ ነበር። ኬዎርኮፍ የፈረንሳይ እና የኢትዮጵያ መንግሥቶች የክብር ኒሻን ተሸላሚ እንደነበርም የወቅቱ ጋዜጦች ዘግበዋል።
በ1919 ዓ.ም. ደግሞ የኢትዮጵያ ውስጥ አርመን ኮሚኒቲ ፕሬዝዳንት ሆኖ አገልግሏል። ቀደም ብሎም በ1915 ዓ.ም. በአርመን ፖለቲካ ልዩነት የተነሳ ሶስት ቦታ ተከፋፍሎ የነበረውን የአርመን ትምህርት ቤቶች በማዋሃድ አንድ ዘመናዊ ትምህርት ቤት (National Armenian Kevorkoff School) ብሎ ሰይሞ አቋቁሞት ነበር። እስካሁንም ይህ ትምህርት ቤት በአራት ኪሎ አርመን ሰፈር አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል። እንዲሁም የኢትዮጵያ ባንክ (Bank of Abyssinia) ቦርድ አባል እና የሎተሪ ኮሚሽን አማካሪ ሆኖ አገልግሏል።
በጣልያን ወረራ ዋዜማ ኬዎርኮፍና ሌሎች የውጭ ሀገር ዜጋ ነጋዴዎች በአንድነት ግማሽ ሚሊዮን ብር አዋጥተው ለኢትዮጵያ የጦርነት ወጪ ድጋፍ ይሆን ዘንድ ለቀዳማዊ ኀይለሥላሴ አበርክተው ነበር። ይህንንም ብርሃንና ሰላም ጋዜጣ በታህሳስ 2 1928 ዓ.ም. እትሙ ዘግቦታል።
በ1928 ዓ.ም. ጣልያን አዲስ አበባ በገባ ጊዜ በፈረንሳዊነቱ ምክንያት ንብረቱ በሙሉ “የጠላት ንብረት” ተብሎ እንደተወረሰበት ይነገራል። በዚህም የተነሳ ወደ ፈረንሳይ ተሰዶ፣ በማርሴይ ውስጥ እንደሞተ ይነገራል።
ታዲያ እሱ ቢያልፍም፣ አሻራውን በአዲስ አበባችን ኪነ ሕንጻ ላይ ትቶልን አልፏል።
.
የጽሑፍ ምንጮች
- “The City and Its Architectural Heritage Addis Ababa 1886-1941” by Fasil Giorghis and Denis Gerard
- “Old Tracks in the New Flower – A Historical Guide to Addis Ababa” by Milena Batistoni and Gian paolo Chiari
- “L’Empire D’Ethiopie : le Miroir de l’ethiopie moderne 1906-1935” by Adrien Zervos
- “ይምጡ በዝና፤ አዲስ አበባ” በያሬድ ገብረ ሚካኤል (1958 ዓ.ም)
- “Urban Africa: Changing Contours of Survival in the City” by Abdou Maliq Simone & Abdelghani Abouhani
- “Out of Africa and into America, The Odyssey of Italians in East Africa” by Enzo Centofanti
- “Moderns Abroad: Architecture, Cities and Italian Imperialism” by
- “La fanfare du Négus” by Boris Adjemian
- “The Dramatic History of Addis Ababa The Capital’s Armenians” by Richard Pankhurst
- “ብርሃንና ሰላም ጋዜጣ” – ግንቦት 29 1927፣ መጋቢት 29 1919፣ ሐምሌ 21 1919 እትሞች
- “አእምሮ ጋዜጣ” – መጋቢት 14፣ 1921 እትም
- “አጤ ምኒልክ በሐገር ውስጥ የተጻጻፏቸው ደብዳቤዎች” በጳውሎስ ኞኞ 2003 ዓ.ም.
የኢንተርኔት ምንጮች
- http://armenianweekly.com/2015/05/06/remembering-the-armenians-of-ethiopia/
- http://www.failedarchitecture.com/le-corbusiers-visions-for-fascist-addis-ababa/
- http://www.africantrain.org
- https://gasparesciortino.wordpress.com/
- http://senato.archivioluce.it/senato-luce/home.html
- http://www.samilitaria.com/SAM/
በርቱ የምታቀርቧቸው ፈርጀ-ብዙ ኪናዊ ስራዎች በጣም አስተማሪ እና ጠቃሚዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ኣመስግኛለሁ!
LikeLike
Thanks Hiwot. You have made me realize my ignorance about the world of architecture. I’m still ignorant but at least I know some of the vocabularies used to describe a building so I could qualify for being ጥራዝ ነጠቅ
LikeLike