አስኮ ጌታሁን እና ዝምታ
(ክፍል ሁለት)
በአዳም ረታ
.
(ከክፍል 1 የቀጠለ)
፫
የአስኮ ጌታሁን አጭር ታሪክ ኪነ አገነባብ ሁለት ፈርጆች አሉት። የቦታና ተውላጣዊ/ሰዋስዋዊ አንጻር። በቦታ ደረጃ ድርሰቱ በሁለት ስፍራዎች ዙርያ (ወሎና አዲስ አባ) የሚያውጠነጥን ነው። የመጀመሪያው ክፍል እንደ አሁን ጊዜ ሆኖ የሚያነሳው ተክለ ሃይማኖት/አዲስ አባን ነው (ሰሌዳ ሀ)። ከመሐል በምልሰት (ሰሌዳ ለ) ትረካው ወሎ ይገባል፤ መደምደሚያ ላይ (ሰሌዳ ሀ’) አዲስ አባ ይመልሰናል።
ሌላው የድርሰቱ ማራኪ ኪን ተራኪው በወሰደው ሁሉን አወቅ ግን ገለልተኛ አንጻር መነሾ የተፈጠረ (እላይ ከተነሳው የስፍራ አሸናሸን ጋር የተያያዘ) በ‘አንተ’ እና በ‘አንቱ’ ተውላጠ ስሞች መከፈሉ ነው። በዚህ የአገነባብ ስልት አስኮ ጌታሁንን በሁለተኛ መደብ ተውላጠ ስም ‘አንተ’ እያለ እየጠራ የሚተርከው የመጀመሪያው ክፍል (ሰሌዳ ሀ/ሀ’) ሲሆን፣ ሌላው ደሞ በምልሰት የጊዜ ክበብ የሚነቃነቀው አስኮ ‘አንቱ/እሳቸው’ እየተባለ የሚጠራበት ሁለተኛው ክፍል (ሰሌዳ ለ) ነው።
‘አንተ’ እና ‘አንቱ’ በስብእናው ዝቅተኛነት፣ የአካባቢው ኗሪ ለአስኮ ጌታሁን የሚሰጠው ስያሜ ነው። አስተማሪ ሆኖ እያለ ‘አንቱ’ ሲባል፣ ከእስር ተፈቶ እንደ እብድ በተቆጠረ ጊዜ ‘አንተ’ ይባላል። ደራሲው በዚህ ግንዛቤ መሐል ገብቶ ሊያርመው አልሞከረም። አንቱና አንተ ካለመተዋወቅና ከመከባበር ጉዳይ ጋር የተያያዘ ብቻ አይደለም። የተራኪው/ደራሲው ገለልተኛነትና አስኮን ‘እንደሚኖረው’ ለማሳየት የተደረገ ጥረትም ነው።
እርዝመታቸው እንዲህ ነው። የመጀመሪያው ክፍል (ሰሌዳ ሀ) በአስራ ሰባት አንቀጾች ሲቀርብ ሁለተኛው የምልሰት ክፍል ደሞ (ሰሌዳ ለ) በአስራ ሁለት አንቀጾች ይቀርባል። ሶስተኛው ‘መዝጊያ’ ክፍል (ሰሌዳ ሀ’) አንድ አናሳ አንቀጽ አለው። በጊዜ እቅድ ከአሁን-ጊዜ ወደ ፊት-ጊዜ መስመራዊ (Linear) በሆነ መንገድ ተራኪው ድርሰቱን ማዋቀር ቢፈልግ በቀላሉ የክፍሎችን (ሰሌዳዎችን) ቦታ ወደ (ለ–ሀ–ሀ’) ማለዋወጥ ይችላል።
ግን እንዲህ አላደረገም፤ ምክንያት ይኖረዋል። ምናልባት ወደ ኋላ ለምን እንዳደረገ ግምት እወረውራለሁ።
፬
በትረካ ትወራ (Narrative Theory) ስለ መተረክ ዘዴዎች ብዙ ዓይነት ክርክር አለ። አንዳንድ መሠረታዊም ይሁን አይሁን አለመግባባት ቢኖርም ብዙ ጊዜ በተለያየ አመዳደብና የአትኩሮት ደረጃ የሚያነሷቸው አራት ዘዴዎች አሉ። ገለጻ (Description)፣ ሪፖርት (Report)፣ ንግግር (Speech) እና ግምገማ (Comment)።
በ”አስኮ ጌታሁን” ውስጥ ያሉትና የተገነዘብኳቸው የትረካ ሞዶች (ዘዴዎች/ስልቶች) ሶስት ናቸው። እነሱም ገለፃ፣ ሪፖርትና ንግግር ናቸው። ይሄ አመዳደብ ወሳኝነት/መጣኝነት ቢኖረውም አስኮ ጌታሁንን ለማንበብ የሚለግሰኝ እርዳታ በቂ ስለሆነ ተፎካካሪ አመዳደቦችን ላነሳና የማያስፈልግ ንትርክ ውስጥ ራሴን ልዶል አልሻም።
ከነዚህ ከሶስቱ በአስኮ ጌታሁን አጭር ታሪክ ውስጥ በጣም በዝቅተኛ ቦታ የተመዘገበው ንግግር ነው። ስለ ዝምታ ካነሳሁ ላጤናቸው የሚገቡኝ ሞዶች ንግግርና ሪፖርት ይሆናሉ። ሪፖርት ስል ምን ማለቴ ነው? ንግግርስ?
ሪፖርት ስል በሰው ልጅ የተደረገ ነገር በተራኪው ሲገለጽ ነው። እነዚህ ድርጊቶች ጉልህ የሆነ ወይም ያለሆነ መቼት ሊኖራቸው ይችላል። ንግግር ስል ደግሞ የልብወለድ ገጸ ባሕርይው (አስኮ) ሲናገር በትእምርተ ጥቅስ (“…”) የሚቀመጠው ነው። እንዲህ በቀጥታ የሚናገረው ብቻ ሳይሆን በሃሳቡ የሚያስበውና ስለ ሃሳቡም የሚያስበው (Perception/Apperception) በዚህ ውስጥ ይጠቃለላሉ።
ንግግር በጊዜ ውስጥ የሚሆን ነው፤ ንግግር የቅርብ እርቀት ነው። ሪፖርት ግን ሩቅ ነው።
ንግግርና ሪፖርት ከዘዴዎቹ ሁሉ ንቁ (Active) የሚባሉት ናቸው። ምክንያቱም ባህርያቸው ውስጥ ድርጊት (Action) አለ። የትረካ ፍሰት ዝርዝር በሌላቸው (ዝርዝር አዘግዪ ነውና) ሪፖርትና ንግግር ሲቀርብ ፈጣን ይሆናል። በ”አስኮ ጌታሁን” ትረካ ውስጥ ሪፖርትና ንግግር ተያይዘውና ተወስውሰው የተሰሩ ናቸው። የጌታሁን ደቃቃ ንግግሮች ከሌሎች ዘይቤዎች ጋር ያለ ማስጠንቀቂያ ይመጣሉ።
የ”አስኮ ጌታሁን” 30 አንቀጾችን በነዚህ ዘዴዎች/ሞዶች ስር ልንመድባቸው እንችላለን። በአንቀጽ ብቻ ሳይሆን ድርሰቱን በሐረግና በቃላት ደረጃ በመክተፍ/በመሸንሸን ዝርዝር ሥራ መስራት ይቻላል። የዚህ ንባብ ዓላማ ግን ስለ አጭር ድርሰቱ አጠቃላይ ስሜት ለመውሰድ ብቻ የምናደርገው ስለሆነ ትርፍርፍ ዝርዝር ውስጥ አንገባም።
ከላይ በጠቀስኩት የሞድ ስየማ ንባቤን ስጀምርና የአስኮን ዝምታ በተጠቀሰው አመዳደብ ልፈትሽ ስሞክር ከታች ያለውን አይነት የመረጃ አሰባሰብ መንገድ ተጠቅሜ ነው። ድርሰቱ በሰላሳ (30) አንቀጾች የተከፋፈለ ነው ብለናል። እነዚህን አንቀጾች የትንታኔ አሐድ አድርገን በመውሰድ በመጀመሪያ በእያንዳንዱ አንቀጽ የትኛው ዘዴ (‘ንግግር’ ወይ ‘ሪፖርት’) ተጠቃሽ እንደሆነ የሚያሳይ ሰንጠረዥ እንሰራለን።
የሞድ ካርታ ሰንጠረዥ
ከላይ በሰንጠረዥ የቀረበው በመጠኑ የተጣራ መረጃ ስለተነሳንበት ጉዳይ የሚነግረን ሀሳብ አለ። በየአንቀጾቹ ‘ንግግር’ የሚቀርብባቸው መንገዶች ሁለት ናቸው። አንደኛው፤ በቀጥታ ተራኪው “አስኮ እንዲህ አለ” ብሎ በትእምርተ ጥቅስ የሚያስቀምጠው (“አስኮ አለ”)፣ ሁለተኛው፤ በሌላ ሰው ወይም ሰዎች በኩል አስኮ ‘እንዲህ አለ’ ወይም ‘ተባለ’ ወይም ‘ይባላል’ ተብሎ የተደነገገውን ነገር ነው (“ ‘አስኮ አለ’ ተባለ”)።
በሰንጠረዡ ውስጥ የምናየው የ‘ሪፖርት’ ገናናነትን ነው። የአስኮ ንግግር የሚመዘገበው በአብዛኛው በዚህ ዘዴ ስር ነው። አስኮ መናገሩ ብቻ አይደለም። ‘ምን ያህል ተናግሮአል?’ ብለን መጠየቅም አለብን። በሌላ በኩል አኀዝ (Quantity) ለብቻው የጥልቀትም መለኪያ አይደለም። የጥራታዊ ፈረጁንም (Quality) መርሳት የለብንም።
ጃርሶ አትኳሪ ጸሐፊ ነው። ደስ የሚል ገላጭም ነው። ግን አስኮን ከንግግር ያወጣው ምክንያት ቢኖር ነው አልኩ። ገጾቹን በመጨመር ስለ አስኮ በተዘረዘረ መልክ ሊነግረን ይችል አልነበር? ከአዲስ አባ በኋላ ወ/ሮ ስህን ሲያስተምር በትምህርት ቤት፣ በመንደሮች፣ በፍርድ ቤቶች በእስር ቤቶች ስለነበረው ሕይወቱ ጥልቅ ወሬ ማምጣት ይችል አልነበር? ለምን አላደረገውም?
ጌታሁን አስተማሪ ነበሩ/ነበረ። ከብዙ ሰዎች ጋር በሀሳብ ተከራክረዋል፣ ተጣልተዋል፣ ተኮራርፈዋል ፍርድ ቤት ተከሰው ቆመዋል። አስራ ስምንት አመት እስር ቤት አሳልፈዋል። መቼም ሳይከራከሩ ዘብጥያ አልወረዱም። ለማስተማር ሲቆሙ ቃላት ከአፋቸው ሳይወጣ አልቀረም። ለምን ግን አስኮ ሲነጋገር እንድንሰማው አልተደረገም? በአስራ ሁለት ገጾች ውስጥ ድምጹን የምንሰማው ጥቂት ቦታዎች ነው።
በቃላት ደረጃ ቆጠራ ብናደርግ ደሞ ከ2,520 በላይ ቃላት ባሉት ድርሰት ውስጥ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ (አሉ/አለ የተባለው ሁሉ ተጨምሮ) የተናገራቸው በቃላት ብዛት 133 ይሆናሉ። በመቶኛ አምስት (5%) ቢሆን ነው። ይሄ አንጻራዊ አኀዝ የሚያሳየን የንግግርን ጠባብ ቦታ ነው።
የዚህ ጽሑፍ ንባብ ማዕከልም ‘ለምን ይሄ/እንዲህ ሆነ?’ የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ መሞከር ነው።
ረዥም የተባለው ንግግሩ በመጀመሪያው ክፍል (ሰሌዳ ሀ) ውስጥ በመንገድ ላይ ከአንድ ባልና ሚስት ጋር ያደረገው (በአንቀጽ 10 እና 11) በአንደበት መላከፍ ነው። እንዲህ ስል የንግግሩን ዘይቤ ዘንግቼም አይደለም። በተራኪው ሪፖርት ካልተደረገ በስተቀር አስኮ ጌታሁን ተክለሃይማኖት ጫማ ሰሪ ሆኖ ከመቀመጡ በፊት ስለነበረው ሕይወቱ አንዲት ቃል እንኳን አይተነፍስም።
አስኮ ተናገራቸው የተባሉት ይዘታቸው የተለያየ ነው።
በአስተማሪነት ዘመናቸው (ሰሌዳ ለ) የሚናገሩት ቁም ነገር እንደሆነ ቢነግረንም በተራኪው ቀጥታ ሪፖርት የተዘገበው ለልጃቸው የተናገሩት አንዲት አረፍተ ነገር ብቻ ናት፤ “እዛ ጓዳ ሂድና አጥና” (አንቀጽ 21)። ይሄ ቀላል አባባል ስለ ትምህርት አስፈላጊነት (“አጥና”)፣ ትምህርት ገለል ያለ ትኩረት የሚጠይቅ ልፋት እንደሆነ (“እዛ ጓዳ”) እና ስለ አኗኗራቸው/ቤታቸው ፕላን (“ጓዳ”) የሚነግረን ነው።
በሌላኛው ክፍል (ሰሌዳ ሀ) ግን አስኮ ንክ በመሆናቸው ሳይሆን አይቀርም (‘እብድና ዘመናይ የፈለገውን ይናገራል’ በሚባል ስልት) ንግግሮቹ በአብዛኛው ‘ግልፅ’ እና ‘አሽሟጣጭ’ ናቸው። ሁለት ምሳሌዎች እንውሰድ፤
- “ዓለም ሰፊ አፍ፣ ሰዎች ሁሉ ጥርሶቿ ይመስሉኛል” (አንቀጽ 12)
- “እንዴት ሁለት የግራ እግር ጫማ ታደርጊያለሽ ልጄ? እግዜር በቅጡ አልፈጠረሽም ልበል?” (አንቀጽ 15)
እነዚህ የተለያየ ዘይቤ ያላቸውን መልእክቶች በአንድ አኀዝ ውስጥ አስተባብሮ አንጻራዊ መቶኛቸውን ማውጣት ደግ አይደለም። ቢሆንም ንግግር ናቸውና ቆጠራው ሲሰራ አንድ ላይ ከመደበል አያመልጡም። ብዙ ጊዜ የአስኮ ንግግር በውይይት (ዲያሎግ) መሀል ስለማይከሰት “ምን አጋጥሞት ወይም ተብሎ ነው ይሄን የተናገረው” ብለን ወደ ኋላ ስንሄድ ጽንብር የለሽ (Indeterminate) ጉዳይ ይሆንብናል።
ለምሳሌ፣ ከላይ በቁጥር ሁለት (አንቀጽ 15) የተናገረው የሰፈሩን ሰው ጠቅሎ ስለሚጠላ ነው? ልጅቷን ስለማይወዳት ነው? ልጅቷስ በእርግጥ ሁለት የግራ ጫማ አምጥታ ነው ወይስ ሊተርባት ፈልጎ? ከልጅቷ ጋር ቀደም ሲል በመንገድ ላይ ተሰዳድበው ይሆን? ወዘተ የመሳሰሉትን ጥያቄዎች እንድናነሳ እንገደዳለን። ታዲያ በአስኮ ታሪክ አሳዛኝነት (በትረካው ውስጥ) ተገፋፍተን ለእሱ የሚያዳላ መደምደሚያ ላይ መድረስም የለብንም።