“ኀሠሣ” (ልብወለድ)

“ኀሠሣ” (ልብወለድ)

በሕይወት ታደሰ (ትርጉም)

.

(ድርሰት በሕይወት ተፈራ)

.

[በደራሲዋ መልካም ፈቃድ ለአንድምታ የቀረበ]

.

.

አንድ

ጠንቅቄ እማውቀው ነገር ቢኖር ተሕይወት የተማርኹትን ነው። ልጅ ኹኜ ነፍስያዬ አንዳች ነገር ስትናፍቅ ትዝ ይለኛል።

ቀኑ መቸም አይረሳኝ። በመስከረም 1860 አንድ ማለዳ ላይ ደሮ ሳይጮኽ ነቃኹ። ጎጇችን ተሌሊቱ የጭለማ ድባብ ገና አልተላቀቀችም። ክንዶቼን ተንተርሼ፥ የጎጇችን ባጥ ላይ አፈጠጥኹ።

ተመቅጽበት የታላቅ ክብር ራእይ በፊቴ ውልብ አለብኝ። የተማረና ትልቅ ሰው ኾኜ እሚያሳይ ምስል ዐይኔ ላይ አለፈ። ዋሸራ ተሚባል ሩቅ ስፍራ ወደ ቤቶቼ መጥቼ መኾኑ ነው። እናቴ ገና ስታየኝ ምድሪቱን ለመሳም በጉልበቷ ተንበረከከች።

የምንደራችንም ሰዎች ተመኻከላቸው የወጣውን ሊቅ በታላቅ አክብሮት ለመቀበል ወደ ቤታችን ጎረፉ። ሴቶች ዕልልታቸውን አቀለጡት፤ ወንዶችም እግዚአብሔርን ስለማይለካው ደግነቱ አወደሱት።

የቀድሞዎቹ እረኞች ባልንጀሮቼ በመንፈሳዊ ቅናት እየተቁለጨለጩ ተመለከቱኝ። አባቴ ለእኔ ክብር ሲል የሰባውን ሙክቱን መርጦ አረደልኝ።

ይኽ ነገር ራእይ ነበር፤ ወይስ ኅብሩ ገና ያልተገለጠልኝ የተስፋ ኪዳን?

ዐይኖቼ ተርገበገቡ።

በዚያው ቅጽበት እነኚኽ ብልጭታዎች ተበታተኑና በቦታው አባቴ ተከሠተ፤ በእኔና እየተሰወረ ባለው ምስለ ራእይ መኻከል ታለው ቦታ የተናገራቸው ቃላት ጀሮዬ ላይ አቃጨሉ፤

“ሕይወትኽ የተሳሰረው ተትምህርት ጋር ሳይኾን ተመሬት ጋር ነው”

በዚኽ አባባሉም የሕይወት አቅጣጫዬን ሊወስንልኝ ቆርጦ መነሳቱ ገባኝ። ወዲያውኑም በውስጤ አንዳች የእምቢተኝነት መንፈስ ተነሳሳ።

አባቴ ጉዳዩን ሲያውቅ መናደዱ አይቀርም፤ ግን ደግሞ ቆይቶ ሐሳቡን ይለውጣል እሚል ማባበያ ምክንያት ለራሴ አቀረብኹ። አሁኑኑ ይኽን አገር ለቅቄ መውጣት አለብኝ አልኹ ለራሴ።

ወዲያው ግን እናቴ ያየችው ሕልም ትዝ አለኝ። እናቴ ስለኹሉም ነገር ሕልም ተማየቷም በላይ አብዛኛው እውን እንደሚኾን ትምላለች። ይኸን ራእዬን ተማየቴ አንድ ቀን በፊት፥ ፊቷ በቅርታ ፈገግታ ተሞልቶ፤

“በሕልሜ የኾነ ሰው ተጀርባዬ ኹኖ ሰርመዲ ነገር ራሴ ላይ ሲጠመጥምልኝ ታየኝ። ማን እንደኾነ ለማየት ዞር ስል አንተው ራስኽ ነኽ። ጠራኹኽ፤ ነገር ግን ፊታቸውን ኹሉ በደንብ ለይቼ ማየት እሚቸግረኝ ብዙ ሰዎች መሀል ገብተኽ ተሰውርኽብኝ። የልጀን ጠባይ አሳምሬ ባላውቅ ኖሮ ትተኸን ልትኸድ ነው ብዬ አሳብ በገባኝ ነበር” አለችኝ።

ምናልባትም ታይቷታል!

ለዋናው እቅዴ ዕንቅፋት ትኾንብኛለች ብዬ ሳይኾን፤ በዚያች ቅጽበት ተእንቅልፏ ብትነቃ ቢያንስ ያን ቀን ለማድረግ ያሰብኹትን ታከሽፍብኛለች ብዬ ነበር የተደናገጥኹት። የዚያ የዕውቀት እና የክብር ካባ የደረበው ሰው ምስል እንደገና ብልጭ አለብኝ።

እመር ብዬ ተነስቼ ቆምኹ፤ ብልጭታውን መጨበጥ እንዳለብኝ በፍጥነት ተገንዝቤያለኹ።

***

በችኮላ ለምዴን፣ የአባቴን ጋቢ፣ ቅምጫናዬን እና የእረኛ ብትሬን አሰባሰብኹ።

ስጋት እንደተላበስኹ ወላጆቼን ተመለከትዃቸው። ተእኔዋ መደብ በተቃራኒ በኩል ታለው መደብ ላይ ተኝተዋል። ቀስ ብዬ በጥንቃቄ ወደ ጉበኑ እያመራኹ ሳለ አባቴ በእንቅልፍ ልቡ ሲባትት ሰምቼ፥ ለአፍታ ባለኹበት ድርቅ ብዬ ቆምኹ።

እናቴም ተገላበጠች። ጥቂት ባለኹበት ቆየኹ፤ ነገር ግን አልነቃችም ነበር። የበሩ ሳንቃ ድምጽ እንዳያሰማ ቀስ አድርጌ ከፈትኹና ወደ ደጅ ወጣኹ።

ወይ እናቴ ወይ አባቴ፤ ወይም ደግሞ ኹለቱም ነቅተው ቢሆንስ ኖሮ ብዬ አሰብኹና አንዳች ቀዝቃዛ ስሜት በሰውነቴ ኹሉ ተሰራጭቶ እንደማንዘርዘር አደረገኝ። የነቁ እንደኹ ከብቶቹን ለማሰማራት ሰዓቱ ገና መኾኑን ያስታውሱኛል። እኔም ወደ መኝታዬ እመለሳለኹ፤ ጓደኛዬ በላይም ጥሎኝ ይኸዳል።

ዕቅዴን ውሃ በላው ማለት ነው።

ውጭ ራሴን ለማረጋጋት የግድግዳውን ምርጊት ደገፍ ብዬ ቆምኹኝ። ውሻችን እያነፈነፈ ወደኔ መጣ። ብትሬን ቃጣኹበትና አበረርኹት። ድምጽ እንዲያሰማ አልፈለግኹም። እያለቃቀሰ ጉበኑ ላይ ተጠቅልሎ ተኛ።

እኔም ዙሪያ ገባውን ኹሉ አንድ ጊዜ ቃኘኹ። ተወልጄ ያደግኹት እዚች ጎጆ ውስጥ፤ እዚኽ በቁጥቋጦ የተከበበ ቀዬ ውስጥ ነው። የወተት ጥርሴን ነቅዬ ንቃዩን የቀበርኹት እዚኹ ነበር።

እናቴ ተጎኔ ቆማ አጥልቄ እንድቆፍር ስትነግረኝ ትዝ ይለኛል። ለሰስ ያለ ፈገግታ ፊቷን አፍክቶታል። “ደሮቹ ጭረው እንዳያወጡብኽ እኮ ነው” አለችኝ። እኔም ተጉድጓዱ ተጨማሪ አፈር ቆፋፍሬ አወጣኹና ጥሪቴን አርቄ ቀበርኹት።

እምወዳትን ጥጃ ለመሰናበት ወደ በረቱ አቀናኹ። እንቅልፍ አሸልቧታል። ተዚኽ በኋላ ግጦሽ እንደማላሰማራት ሳስታውስ ልቤ ተሰበረ። እሷም አንዳች የተሰማት ስሜት ነበር መሰል፤ የዐይኖቿ ሽፋኖች በድካም ገርበብ እንዳሉ በጥርጣሬ መንፈስ ገረመመችኝ። ዐይኖቿ “በቃ ይኸው ነው? ጥለኸኝ መኸድኽ ነው?” እሚሉ ይመስላሉ።

በኀዘን እንዳቀረቀርኹኝ ፊቴን አዙሬ በረጃጅሙ ተራመድኹ።

ጨክኖ መኸዱ ይኾንልኛል? ዳግመኛስ ወዲኽ እመለስ ይኾን? ወላጆቼን እንደገና ለማየት እታደል ይኾን? ስመለስስ ጥጃዬን አገኛት ይኾን? እያልኹ ራሴን ጠየቅኹት።

ሐሳቤን እንዳልቀይር በመፍራት በሩን ከፍቼ ተፈተለክኹኝ።

***

ሕይወት ታደሰ (ትርጉም)

(ድርሰት) – ሕይወት ተፈራ

.

[በደራሲዋ መልካም ፈቃድ ለአንድምታ የቀረበ]

.

[ምንጭ] – “ኀሠሣ”። 2009 ዓ.ም። ገጽ 1-3።

.

4 thoughts on ““ኀሠሣ” (ልብወለድ)

  1. ” ጎሠሣ ” ምን ማለት ይሆን አማርኛ አውቃለሁ ብየ እገምታለሁ የዚህ ቃል ትርጉም ግን አልገባኝም:: የ ” Mine to Win ” ትርጉም ጋር አልመሳሰልልህ አለኝ ትርጉሙ ” የእኔ ማሸነፍ ” ነው አይደለም ? ከተሳሳትኩ እታረማለሁ::

    Like

    1. የኀሠሣ ትርጉም – ፍላጎት ፍለጋ ጥያቄ ጥየቃ
      ምርምር መርመራ ፈቃድ መፍቅድ ሐሳብ
      ምኞት፡፡ ብየ ኅሠሣ እምኂሩትክሙ፡፡

      Like

አስተያየት ለመስጠት