“ቆይታ ከመሐመድ ኢድሪስ ጋር”
(ቃለመጠይቅ)
.
[ከአንድምታ ጋር የተደረገ ውይይት]
.
[አብዛኞቻችን መሐመድ ኢድሪስን በተወዳጁ “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ በሚያቀርባቸው አጫጭር ልብወለዶቹ እናውቀዋለን። ከአጭር ልብወለዶች ባሻገር በርካታ የፊልም ጽሑፎችን ደርሷል። ባለፈው ዓመትም “ሣልሳዊው ዐይን” የተሰኘ ግሩም የአጭር ልብወለዶች ስብስብ መጽሐፍ አሳትሟል። አንድምታ መሐመድን በቅርቡ በሥነጽሑፍ ዙርያ አነጋግራው ነበር።]
.
እስቲ ስለ ልጅነትህ ትንሽ ብታጫውተን?
የልጅነት ጊዜዬ፣ በጣም ወርቃማ ነበር። የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያስተላልፋቸው የነበሩትን “ሙን ላይቲንግ”፣ “ፔሪ ማሰን”፣ “ትዋይላይት ዞን” የመሳሰሉትን ተከታታይ ፊልሞች እያዬሁ ነበር ያደግሁት።
ሰፈሬ አምባሳደር ሲኒማ ቤትም እገባ የነበረው፣ ከስድስት እስከ ዐሥራ ኹለት ሰዐት፥ ሦስት ፊልም፣ በሦስት ብር፥ በነበረበት ጊዜ ነበር። የቻርለስ ሑስተን እና የዮል ብሬነርን “ዘ ቴን ኮማንድመንት” ከሠላሳ አምስት ዓመት በፊት ነበር ያዬሁት። ያኔ ያዬኋቸው ፊልሞች፣ የሥነ ጽሑፍ እና የሲኒማ ፍቅር፡ እንዲሁም ደግሞ፥ ዕውቀት ሰጥተውኛል።
የመጀመሪያ አጭር ልቦለዴን የጻፍሁት፣ ስድስተኛ ክፍል እያለሁ ሲኾን፤ “ፀሐይን የጎበኘው ሰው” የተሰኜ ሳይንስ ፊክሽን ነበር።
ከ “አዲስ አድማስ“ ጋዜጣ ጋር እንዴት ግንኙነት ጀመርክ?
እኔ፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ፥ መጻፍ የጀመርሁት በ1993 ዓ·ም ነው። የመጀመሪያ ጽሑፌም፣ “ውዱ ስጦታ” የሚል አጭር ልቦለድ ነበር። በዛ ወቅት፣ አሰፋ ጎሣዬ በጣም ያበረታታኝ ነበር።
ወደ አጭር ልብወለድ ደራሲነት እንዴት ልታመዝን ቻልክ?
የአጭር ልቦለድ ጸሐፊ የኾንሁት፣ አስቸጋሪና ጥበብ የሚጠይቅ የሥነ ጽሑፍ ዘርፍ ስለኾነና ስለሚያስደስተኝም ጭምር ነው። የታሪኮቼ ፍሰት፣ እንደፊልም የሚኾነው፥ ስጽፍ የሚታዬኝ፡ እንደዛ ስለኾነ ነው።
“ሣልሳዊው ዐይን“ የተሰኘው መጽሐፍህ አዘገጃጀት ሂደት እንዴት ነበር?
“የሣልሳዊው ዐይን” ዝግጅት፣ በጣም ጥሩ ነበር። በዋናነት፣ ከዚህ በፊት ጋዜጣ ላይ ወጥተው የነበሩትን ታሪኮች፣ ማስፋት ያስፈልግ ነበር። አድካሚ ቢኾንም፤ አስደሳች ነበር። ጥሩ ኤዲተር ስላገኘሁ፥ ሥራው፣ ሊሳካ ችሏል።
“የእኩለ ሌሊት ወግ“ እና ”የጉንዴ ቀለበት“ የተሰኙት ልብወለዶችህ ጀርባ ስላለው ታሪክ እስቲ ብታጫውተን …
“የእኩለ ሌሊት ወግ” የተጻፈው፣ «የሰው ልጅ ዕጣ ፋንታ፣ በፈጣሪ የተጻፈ ነው» ከሚለው፣ የእስልምና አስተምህሮ፥ ተነሥቶ ነው። “የጉንዴ ቀለበት” ደግሞ፣ ከራሴ የግል ሕይወት ተነሥቼ፥ የጻፍሁት ታሪክ ነው። ጉንዴ፣ በኔ ሕይወት ውስጥ ያለች፥ ጓደኛዬ ነች። ጉንዴን፣ በአጭር ልቦለድ መጻፍ፥ ከባድ ቢኾንም፤ ለማሳየት ግን ሞክሬያለሁ።
ከቀጣይ ስራዎችህስ ምን እንጠብቅ …የትኛውስ ቀድሞ ይወጣል?
በቅርቡ፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ የወጣ፥ “ሞያተኛው ቀብር አስፈጻሚ” የተሰኘ አጭር ልቦለድ አለ። በቀጣይም፣ “የበጋዋ እመቤት” በሚል ርእስ፥ ሌላ አጭር ልቦለድ ይቀጥላል። ከአኹን በኋላ፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ፥ በየዐሥራ አምስት ቀን፥ ለመጻፍ ዕቅድ አለኝ።
በመጽሐፍ ደረጃ ደግሞ፣ “ሞገደኛው” የሚል ሳይንሳዊ ልቦለድ ለመጻፍ አስቤያለሁ፤ በፈጣሪ ፈቃድ።
እናመሰግናለን።
እኔም አመሰግናለሁ!
.
መሐመድ ኢድሪስ
(ቆይታ ከአንድምታ ጋር)
መስከረም 2010 ዓ.ም
.
ከመሐመድ ኢድሪስ ቆይታ፣
እንዲያው ለአፍታ፣
ለጊዜ ጠብታ፣
በእኛ አድምታ።
ተወያያችሁ፣
ጥያቄና መልስ ተነጣጠቃችሁ፣
ሳትጀምሩ ጨረሳችሁ?
ቆይታ ካሉት ውይይት፣
ጥያቄ ልኮ መልስ ማግኘት፣
ይመዝገብ በዩኒስኮ
ይህ አዲሱ ግኝት።
LikeLike
ለየት ያለ እና ጥሩ ቃለ መጠይቅ ነው፡፡ መሃመድ ኢድሪስን በትንሹም ቢሆን አስተዋውቆናል፡፡
LikeLike