“ዐፅም”
በገብረ ክርስቶስ ደስታ
(1950 ዓ.ም)
.
(ገብረ ክርስቶስ ግጥሙን ሲያነብ ለማዳመጥ)
.
.
ማነህ የተኛኸው?
እንቅልፍ የደበተህ ሥጋህን ጥለኸው።
.
ምን ኖረኻል አንተ?
ንጉሥ ኖረኻል ወይ፣ ኖረኻል ወይ ጌታ
ወይ ቁሩንጮ ለባሽ፣ ለማኙ ከርታታ
ሚኒስትር ደጃዝማች፣ ወይም ፊታውራሪ
ባለብዙ ገንዘብ፣ አሽከር አሳዳሪ
ኖረኻል ወይ አንተ?
አጥንትህ ወላልቆ እንዲህ የሻገተ።
.
ሥራህ ምን ነበረ? ቤትህ የት ነበረ?
እርስትህ የት ቀረ?
የተመራመረ አዋቂ ፈላስፋ
ብዙ መሰናክል ካለም ላይ የገፋ
ሳትሆን አልቀረህም
ጉድ ነው መልክህ የለም።
.
ማነሽ ማነህ አንተ?
ማናችሁ እናንተ?
.
ማነሽ በዘመንሽ የውበት እመቤት
ሆነሽ የገዛሽው የወንዶችን ጉልበት
በክንድሽ ያለቀው
ወጣቱ ጐልማሳ የት ነው የወደቀው?
.
ምን ኖረሻል አንቺ አጥንትሽ ይናገር
እንጨት ተሸካሚ
ወይ ኩበት ለቃሚ
ወይ ልብስሽ ያደፈው ጥሬዋ ባላገር
ወይም ሽቅርቅሯ እስቲ ተናጋሪ
ሽቱሽ የጎረፈው መንጭቶ ከፓሪ
በወርቅና ባልማዝ በሉል እንደሆነ
ተጫውተሽ የሄድሽው ዝናሽ የገነነ።
.
እስቲ ተናገሪ ቋሚ ያዳምጣል
አንቺ ለመሆንሽ ምስክርሽ የታል?
.
ያሻኻል ምስክር
ሞተህ ስትቀበር
ድንጋይ ላይ ተጽፎ የሚናገርልህ
ምልክት የሚሰጥ አንተ ለመሆንህ
ሐውልት የሚያቆይህ
ዘመድ ያስፈልጋል ከሌላው ለይቶ
መንገደኛ እንዲያውቅህ ቆሞ ተመልክቶ።
.
“እገሌ ነው” ብሎ ታሪክ የሚያወራ
እንዲደነቅልህ ቀሪው ያንተ ሥራ
ተነስ አንተው ጥራ!
.
እጐንህ ከተኙት ዐፅሞች በጉድጓድ
አለ ወይ ዘመድህ የምታውቀው ጓድ?
ወዴት ነው አባባ የታለች እማዬ
ጋሼ ወዴት ይሆን የት ቀረች እትዬ?
.
ጠፍቷል ምልክቱ
አጥንትና ሥጋህ ሲሰነባበቱ።
.
ከሙታን ማኅበር በመዝገብ ገብተሃል
ማንኛውም አጥንት አስክሬን ሆነኻል
የሞት ጠባሳ ነህ አስታዋሽ ሥራውን
ከንቱ ነው የምትል አወይ ፍጡር መሆን!
.
የተንቀራፈፈው እጅ እግሩ ሸምበቆ
የተከፋፈለው ሰረሰሩ ለቆ
ጥርሱ ያገጠጠ ዐይኑ የወለቀ
ጐድኑ ተቆጥሮ ጅማቱ ያለቀ
የተገጣጠመ የተሰራ ባጥንት
ሥጋ ወዝ የሌለው የሰው ዘር ምልክት።
.
ሆነህ የተኛኸው
የማትታወቀው …
ምን ኖረኻል አንተ?
.
ገብረ ክርስቶስ ደስታ
.
[ምንጭ] – “የዛሬይቱ ኢትዮጵያ”። መስከረም 10፣ 1950 ዓ.ም።
.
ነፍስ ይማር 😥
LikeLike
It is wonderful to hear GKD’s voice reading his poetry.
LikeLike
wonderful man
LikeLike
አደንቃለሁ!!
LikeLike
Gebre! the real pet and painter! May God bless u again in z heaven.
LikeLike