“ያጼ ዳዊት ጀብዱ”
በደብተራ ኀይሉና በሐጅ አሊ
(1800 ዓ.ም)
.
.
.
ከዚህ በኋላ ከዛር ንጉሥ ሊዋጉ ሔዱ። ገና ሳይደርሱ ላኩባት። ሲልኩባት፣
“በዦሮ የሰሙን በዓይን ሳያዩት አይቀርምና … ታዪን መጣሁ” ብለው ላኩባት።
እርሷም ስትመልስ፣
“የኔም ሰው በነፍጥ ያልቃል። የርስዎም ሰው በሟርት ያልቃል። እኔም አልሞትም እርስዎም አይሞቱ … ምነው በፍቅር ብንለያይ አይሻልም?” ብላ ግብር ሰደደችልዎ።
ከዝያ በኋላ “ክፉ የተናገረች ታየኝን ነበረች!” ብለው ተመለሱ። ከቤታቸው በወጡ በ፯ ዓመት ቤታቸውን ገቡ።
ዳግመኛ የእስክንድርያ ንጉሥ የአሕዛብ ጸላት ቢነሣበት ዜናዎን ሰምቶ ነበርና “መጥተህ እርዳን” ብሎ ላከበዎ።
ተነሡና ሲሔዱ የ፫ ቀን መንገድ እንደሔዱ ዘንዶ እባብ ያለበት አገር ደረሱ። እየረገጡት የሚሔዱ ነው።
ከዚህ በኋላ ቤት የሚያህል አሞራ በኢየሩሳሌም አለ ያነን አስነድተው አመጡት። በእግዜር ፈቃድ ያነን በፊተዎ አደረጉትና ቢሔዱ እባቡና ዘንዶውን እየለቀመው ይሔዱ ዠመረ። የእባቡንና የዘንዶውን ምድር ሲጨርሱ ከደህናው ምድር ሲደርሱ ያም ጠላቱ መምጣተዎን ቢሰማ ሸሸ ‘ይዩልኝ’ ብሎ። የላከውም ሸሸ ‘እኔን ይጨምሩኛል’ ብሎ።
ከዚህ በኋላ ያሰቡትን ሳይደርሱ የማይቀሩ ንጉሥ ናቸው “ቀራንዮን ስሜ ኢየሩሳሌምን አይቼ አመጣለሁና እሔዳለሁ” አሉ።
ሹማንምቱ ገብተው “አይሂዱ ይቅሩ” ብለው መከሩ።
“ተቀረሁ በኢየሩሳሌም ለውዝ ገውዝ የሚሉ ሽቱ አለ ብለውኛልና ልመለስ አምጡልኝ” ቢሉ ሒደው አመጡልዎ ተመለሱ።
ከዚህ በኋላ የንጉሥን ብርታት ቢሰማ የሮም ንጉሥ “ልጅዎን ይስጡን” ብሎ ላከ። ማጫዎን ፵፰፼ መድፍ፣ ነፍጥ፣ ቁጽር የሌለው እቃ የማይታወቅ ሰጠ። ብዙ ነው። እጅግ የሚወዱዋት ልጅ ነበረችና ለርሱ ዳሩዋት።
ሲዘምቱም በ፼ በ፼ ነፍጡ መድፉ እየተቈጸረ ያሲዙ ነበረ። ፵ ፵፼ አኽያ በዳውላ ወርቅ እየተጫነ ከየደረሱበት እያሳመኑ የወርቅ ቤተ ክርስቲያን እየሰሩ፣ ደጅ አዝማች እየሾሙ፣ መምሕር ካህናት እየሰሩ ይሔዱ ነበርና ከባሕር ወዲህ ያለን ሁሉ አገር አሳመኑት። ከኢትዮጵያ ምድር አንድ አልቀረዎም ሁሉን አሳመኑት።
ክፉ ወንድ ልጅ ነበረዎ።
‘እሱ ይነግሣል’ የሚሉ ንግር ነበረና አይወዱትም ነበረ። ሀብተዎን ሁሉ ስለዚህ ምክንያት ለሴት ልጅዎ ይሁን ብለው ሮም ሰደዱት።
“እርሱም በሀብቱ ይንገሥ” አሉ።
እርሱም መጥቶ ነገሠ። የርስዎም እቃ ተመልሶ ሮም ወረደ።
ተፈጸመታሪክዘጸሐፎኃይሉወዘአጽሐፎሐጅአሊ።
.
ደብተራ ኀይሉ እና ሐጅ አሊ
1800 ዓ.ም
.
[ምንጭ] – Bibliothèque Nationale። Eth Ms 144። ቅጠል 19-20።
One thought on ““ያጼ ዳዊት ጀብዱ” (ክፍል 2)”