“የፈላስፋው ውሃ” (ወግ)

“የፈላስፋው ውሃ”

.

.

አንድ ንጉሥ እጅግ አጥብቆ የሚወደው ፈላስፋ ነበረው። አብሮት የሚጋበዝ፣ የሆነውን የሚሆነውንም ሁሉ የሚያማክረው።

በጤናና በስምምነት አያል ወራት አያል ዘመናት ሲኖሩ አንድ ቀን ከገበታ ላይ ለምግብ ተቀምጠው ሳለ ፈላስፋኑ አንስቶ “አዬ!” አለና እጅግ ተከዘ። ወደ ምግቡም እምብዛም ነፍሱ አልፈቀደ። በዚህን ጊዜ ንጉሡ ደንግጦ ያመመው መስሎት “ምነው በደህናህን?” ብሎ ጠየቀው።

ፈላስፋኑ እየመላለሰ ‘አዬን’ ብቻ ያዘ።

ንጉሡም “ደሞ አመመህን?” ቢለው እንኳን “አላመመኝም” ብሎ መለሰለት። “እንግድያውስ አሁንም አሁንም እየተከዝህ ‘አየ’ የምትለው ምን ብትሆን ነው?” ብሎ መረመረው።

ቀጥሎም ‘አዬን’ ብቻ ያዘ።

ንጉሡም ገሚሱ ቁጣ በገሚሱ ጭንቀት “እንደዚህ ያለ ምንድር ነው? ሯ!እባክህን ንገረኝ ምንድር ነው ብልሃቱ?” ብሎ ቢለው

“ክፉ ዘመን የሚመጣብን ቢሆን ነው እንዲህ የምሆነውን የማዝነው” ብሎ ፈላስፋኑ አለው።

የባሰውን ንጉሡ በዚህ ነገር ተጨንቀ። ንጉሡም በፍጥነት ነገሩን እንዲረዳው ፈለገ። ፈላስፋው ግን መልሶ ‘አዬውን’ ያዘ። ተዚህ ወዲህ ንጉሡ አጥብቆ ፈራ። “ሯ! እባክህን ውሃ አታርገኝ ንገረኝ” አለው።

“እስከ ሦስት ዓመት እንደለመድነው ጊዜ ሁሉ ነው። ቀጥሎ ግን የሚዘንበው ዝናብ እስከ ሦስት ዓመት ድረስ ሰውም ሆነ እንስሳም ሆነ ፍጡር የተባለ ሁሉ ይመርዛል። ውሃን የጠጣ ሁሉ ያብዳል። ወንዙ ምንጩ ባሕሩ ዝናቡ ሲዘንብበት ይመረዛልና። ስለዚህ ውሃ የጠጣ ሁሉ ያብዳል። ተዚህ የበለጠ ምን የሚያሳዝንና የሚያስተክዝ አለ?” ብሎ አረዳው።

ንጉሡም እንደ ፈላስፋው አንገቱን ደፍቶ ተራውን ይተክዝ ጀመረ። ቀጥሎ ጥቂት ጥቂት ተንፍሶ “ስማ እንደዚህ ያለ የማይቻል መዓት ሲመጣብነ ጊዜ ምን ይበጀናል?” ብሎ አማከረው።

“ለዚህማ መቼስ ምን አቅም አለኝ! ያሳየኝ ይህ ነው። ባዋጅ ‘የደህናውን ዝናብ ውሃ ጉድጓድ እያበጀህ አስቀምጥ’ ተብሎ ማስታወቅ ይሻል ይመስለኛል … ለክፉው ዘመን መውጫ እንዲሆን” ብሎ የተቻለውን ምክር መከረ።

አዋጁም ሳይውል ሳያድር ተመታ። ከሕዝቡ የፈራ ጉድጓድ ይምስ ጀመር። ነገሩን የናቀ ግን፣

“ተወው! አመሉ ነው። ሁልጊዜም አዋጅ ይመታልና መቼ አንድ ነገር ሁኖ ያውቃል? ደግሞ ያሁኑስ የሚያስደንቅ አዋጅ ነው! ተእግዜር ጋራ ተማክረዋልን? ” እያለ ያፌዝ ጀመር።

ከቤተ መንግሥቱ ደሞ ጉድጓድ ሁሉ ተሰናድቶ ተምሶ የደኅናውን ዝናብ አከማቹበት። በቁልፍም ተቆለፈ። የፈሩትም እንደዚሁ አደረጉ።

ያ ቀን መድረሱ አልቀረምና ደረሰ። ገና መዝነብ ሲጀምር በየወንዙ በየምንጩ በየባሕሩ ሲጥልበት ጊዜ ተመረዘ። ያን ውሃ የጠጣ ሁሉ ማበድ ጀመረ። ሲል ሲል እብደቱ እየባሰ ሄደ። የእብደት ብዛት እየገነነ ሄደ።

ነጋዴ ንግድነቱን ትቶ ወደ ሌላ ሆነ። አራሽም እርሻውን ትቶ ወደ ሌላ ሆነ። ልጅም አባት እየተወ ወደ ሌላ ሆነ። ካህናትም ክህነታቸውን ትተው ወደ ሌላ ሆነ። ቁም ነገር የነበረው ጨዋ ሆነ መኳንንትም ሆነ ሊቃውንትም ውልን ትተው ወደ ሌላ ሆነ። ለእብደቱ ዲካ ጠፋበትና ሁሉም ዝብርቅርቁ ወጣ።

ተዚህ ወዲህ በጐራ በጐራ እየተለየ፣

“ነጋሪት ምንድር ነው? ቆሪ እንጨት አይዶለምን? በሉ ነጋሪቱንም ጠፍሩ! መለከቱንም እምቢልቴውንም አብጁ!” አሉ።

በየጐራው አበጀ። ሁሉም ተተበጀ በኋላ ነጋሪቱን እየጐሸመ፣ መለከቱን እያንጠራራ፣ እምቢልቴውን እየነፋ … ሕዝቡ ሁሉ መቸም አብዷልና፣

“ንጉሥ አልነበረነም ወይ? አለ እንጂ! ወዴት ነው? ከግቢው ተቀምጦ ይንፈላሰሳል!” አሉ።

ይህነን ሁሉ ንጉሡም ፈላስፋውም ያያሉ ይሰማሉም።

ሕዝቡም እንዳልነው ጐራ እየለየ ነጋሪቱን እያስጐሸመ፣ መለከቱን እያንጠራራ፣ እምቢልቴውን እያስነፋ፣

“ንጉሣችን ወዴት ነው? በል ሳብ ወደ ግቢ!” እያለ ይስብ ጀመር።

ገቢዎች ይኼንን ነገር ባዩ ጊዜ በንጉሡ ታዛዥ የግቢ በር ሁሉ እንዲዘጋ ታዘዘ። እነዝያም እብዶች በደረሱ ጊዜ በሩ ተዘግቶ አገኙ።

“ደሞ ዘግቶታልና! አዎን ሊተርፈን? ሯ!” … በድንጊያም በዱላም ያን መዝጊያ ተለቀቁበት።

ንጉሡም ይኼንን ባየ ጊዜ ለፈላስፋኑ “አንተ! እነዚህ እብዶች ሊገሉን ሊፈጁን ደረሱብን! ምን ይበጀን ትላለህ?” ብሎ አማከረው።

“ንጉሥ ሆይ! እኔማ በጉድጓድ ደኅናውን ውሃ እናጠራቅም ለክፉው ዘመን መውጫ እንዲሆን ብየ መክሬ ነበር። ለሕዝቡም ይኼነኑን አስታወቅነ ይሆናል ብየ ነበር። ሳይሆን ሲቀርማ ያነኑ የሚያሳብደውን ውሃ ጠጥተን አንድ እንምሰል!” አለ።

እነሱም ያነኑ የሚያሳብደውን ውሃ ልጅ ተሾልኮ ይሂድና በቅምጫና ይዞልን ይምጣ ተብሎ ሰደዱት። ሄዶ ይዞ መጣ። እንደ ጠበል ተሻምተው ጠጡ። ወዲያውም አበዱ።

ንጉሥ መዝለልና መቀባጠር ጀመረ። ወዲያውም ወደ ግቢው በር ሂዶ፣

“ይኼንን በር ማን አባቱ ነው የዘጋው?” አለ … እርሱ ራሱ ዝጉ ብሎ ሲያበቃ!

ወዲያው ብዋ አርገው ከፈቱ። ንጉሡ እየዘለለ እየለፈለፈ እንደነሱ መስሎ በሩን በወጣ ጊዜ የተሰበሰበው ፍጡር ሁሉ መንገድ ለቆ ገለል ብሎ ዳር እስከ ዳር “እልል!” አሉ። ገሚሱ ያልሰማ “ምንድር ነው ነገሩ?” ብለው ሲጠይቁ፣

“ንጉሣችን አብደው ነበር ሽረዋል” ተባለ … ዳር እስከ ዳር እልልታውን አቀለጠው!

ክፉውን ዘመን ሁሉ ሲያብዱ ኖሩ።

ደኅናው ዘመን ሲገባ ሁሉም እየስፍራው እየሙያው እየደምቡ ገባ። መንግሥቱም አገሩም ሁሉም ረጋ።

.

[ምንጭ] – Major J. Eadie. 1924. “An Amharic Reader”. pp. 29-33.

አስተያየት ለመስጠት

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s