“ጉማ ላሎ” (ግጥም)

“ጉማ ላሎ”

ከሰሎሞን ዴሬሳ

(1963 ዓ.ም)

.

.

ቅኔ ነው ተባለ መሰረቱ

በብራና ቃላት መታሰሩ፤

እየተፍጠረጠረ ዝምብስ ይሞት የለ

እልባት መሃከል፤

ጉማ ሳይከፈል?

.

ቅኔ ነው አላችሁ መሰረቱ

ሰማእታት ከስሜት እንዳልተወለዱ

ቤትና ቤት ማምታታቱ፤

ቡሄ በሉ ልጆች ሁሉ

የቡሄን አደራ አንች አሞራ

.

መነጠር ሆነ ሸለቆ ተራራ

ቋንቋን አርጐ ባላጋራ

ድብብቆሽ መጫወቱ

ማግና ድሩን እያጣጡ

የማይገባ መጣፍ ካልገለጡ …

.

ልግለጥ ታድያ፣ ልግለጥ?

ኦኪ ዶክ …

ሳጠል ቆኜ፣ ፊደል ዋሬ

ቤንቴ ካራማሹኔ፣ ሲቡ ዳርጌ

አቡ ጊዳ፣ ራፉ ጂዻ

ቴኜ ዹግና፣ ኛኔ ሙግና

ሳጠል ቆኜ፣ ወዘተርፈ ለግእዙ

ቤንቴ ካራማሹኔ፣ ሲቡ ዳርጌ … 

ምን ይፈጠር

ልጅነት አይሰቀል

ምን ይፈጠር?

.

ከበሮ ነው ብልስ መነሻዬ

የረኛ ዋሽንት መጓዣዬ

ኰረዳይቱ መድረሻዬ

ያረረ ለቅሶ የራእይ ፊርማዬ

የኰረዳ ምላስ መሰቀያዬ

ብልስ?

ምን ትሆኑ?

ዝግባ አትቆርጡ

ሳታስፈቅዱ

ምን ትሆኑ?

.

በሌባ ጣቴ እምብርቴን

አጥቅሼ

የሌለ ብራና አለስልሼ

እንደ ትግራይ እንጉርጉሮ

ብልስ?

ጉማ ላሎ

ነያ ጉማ ላሎ

ጉማ ላሎ

መንኰራኩር መጣች በጪስ ተሸፍና

ጉማ ላሎ

ነያ ጉማ ላሎ

ጉማ ላሎ

የናትህ ልጅ ደፍታለች አንገቷን፣ ታለቅስልሃለች

ጉማ ላሎ

ነያ ጉማ ላሎ

ጉማ ላሎ

ምሽትህ ድርብ አሸንክታብ አጣፍታለች

ጉማ ላሎ

ነያ ጉማ ላሎ

ጉማ ላሎ

ብታቅማማ፣ ባታቅማማ

አትል ግጥም አይደል

ዱዳ ካልሆንህ የማትሰማ

.

ልጓም ካለ ለፍትወቱ

ሀሳብ ካለ ቸርነቱ

ብትሰማ

ባትሰማ

ብፈነዳ

ባልፈነዳ

ብቀኝ

ባልቀኝ

ባልመቀኝ

ባዳምጥህ ትዝብት ሁነኝ

.

ድንጋይ ሳልቈጥር

ቃላት ሳልቋጥር

ስንኝ ሳላዛውር

ግጥም ነው ቋንቋ ነኝ

ምን ታረጉኝ

.

ሰሎሞን ዴሬሳ

.

[ምንጭ]ልጅነት። ፲፱፻፷፫። ገጽ 41-43።

.

4 thoughts on ““ጉማ ላሎ” (ግጥም)

አስተያየት ለመስጠት