“ባይተዋር የሆነው ብቸኛው ወጣት”
ከዮሐንስ አድማሱ
(1957)
.
.
ባይተዋር የሆነው ብቸኛው ወጣት
ሕሊናና ምኞት የተማቱበት
ተወጥሮ ያለ በሁለት ዓለም
ቆዳው እየሳሳ ነፍሱ ስትከስም፤
ባይተዋር
ባይተዋር
ብቸኛው ወጣት፤
የዘመን ከርታታ ቋንቋ ቸግሮት
ስሜቱን መግለጹ አድርጎ በስልት
ይኸው ተስኖት
ሐሳብ አነሁሎት አይለይም ከንክ
ወይንም በሙያ ወይንም በመልክ።
.
ተቀምጦ በድንገት ይዘምታል ሐሳቡ
ድንገት ሳያስበው ይዝላል ልቡ፤
ወጣቱ
ወጣቱ
የሚኖር በከንቱ፤
ሰው የለውም አሉ፣ በስሙ እንዳልጠራው እንዳይል አቤት
እገሌ እንኳ አይባልም እሱም በዝቶበት፤
ገና ገና
ገና ወጣት ሲሆን ስሙ ጠፍቶበት፤
ይማኩሳል
ይወጣል ይወርዳል
ከቅል እቀንድ ይላል ቃል ስም ለማግኘት
የነፍስ ብዝባዜ የነፍስ ፈተና
ስም አጥቶ ፍለጋ መማታት አገና።
.
ባይተዋር ወጣቱ
የባይተዋርነት ፍጹም አብነቱ
ለስም ብቻ አይደለም ትግሉ ብዙ ነው አለው ብዙ ዋልታ
በነዚህ መካከል ትካዝና ሐዘን ጋርና ዋይታ፤
ባንድ በኩል መስቀል ባንድ በኩል ጦር
ይኸም ተለውጦ መስቀል ከሰላጢን አብሮ ሲጣመር
(ወይንም)
ይህ ይለወጥና አለመቁረጥ ፍዳ
የመዋለለ ዕዳ፤
ባንድ በኩል ደግሞ ማተቡን በጥሶ
ሁሉን ነገር ጥሶ
ይመኛል ሊኖር
ወጣት ባይተዋር።
.
ሁሉንም አንድነት መጨፍለቅ አውኮት
ወይ የራሱን እምነት
(እንዳለው ምናልባት)
ማስረገጥ ቢሳነው ጸንቶ በኔነቱ
(ምናልባት እንዳለው ሰው የመሆን ልዩ … ልዩ ምልክቱ)፤
ገባ ወህኒ አምባ
ገባ ወህኒ አምባ
ባይተዋር ወጣቱ የብቸኝነቱን ዕንቡን እያነባ
ገባ ወህኒ አምባ፤
ኑሮ ከሽልላበት ሥሯ ተመዝምዞ
ፍሬዋ ጎምዝዞ
ፍሬ ፍች አጥቶባት ገባ ወህኒ አምባ
ገባ ወህኒ አምባ።
.
ዮሐንስ አድማሱ
.
[ምንጭ] – “እስኪ ተጠየቁ …”። 1990 ዓ.ም። ገጽ 78-79።