“ቀልድ በመንገድ” (ወግ)

ቀልድ በመንገድ (ወግ)

.

አንድ ተማሪ ትምህርቱን ለመፈጸም ተሸዋ ተነሳ። እስቡ በጐጃም አድርጎ ወዲያው ወደ ጐንደር ገብቶ አገሩን ለመመለስ ነው። ተማሪ ሁሉ ጐጃምንና ጐንደርን ይመርጣል። ሊቃውንት የበዛበት አገር ነው፣ ትምህርት በሰፊው የበዛበት ነው፣ ከዝያ የተማረ ሰው አለቃ ለመሆን ይችላል።

ስለዚህ ብሎ ያልነው ተማሪ ተነስቶ የጐጃምን ድምበር ሲደርስ ሰብል ከመንገድ ዳር አገኘ። ከሰብሉ ዳር ትንሽ ልጅ ተቀምጦ ከሰብሉም ውስጥ ብዙ ዝንጀሮ ተለቆበት ሲያወድም አየ። ለሰብሉ አዝኖ ልጁን

“ልጄ ይኼነን ሁሉ ዝንጀሮ አንተ ነህን እምትጠብቅ” ብሎ ጠየቀው።

ልጁ ምላሽ ሲመልስለት፣

“የኔታ እኔ ጠባቂያቸው ተሆንሁ ተግመሩ ዘጠኙን ተውጭልጭላው አስሩን ይውሰዱ” ብሎ አለ።

ደብቴ እጅግ ተናደደና

“በምን አፍህ ነው እንደዚህ ያለውን ቃል የምትናገር” ብሎ ቢለው

“ታፍንጫየ በታች ተሸንጎበቴ በላይ ነው” ብሎ መለሰለት።

ደብቴ የባሰውን ተናደደና

“እንግዴህ ወዲህ ምን ይሞቱዋል” አለ።

ልጁ ቀበል አርጎ

“ይኼነን ለልጄ ይኼነን ለምስቴ ተብሎ ተናዝዞ ይሞቱዋላ” አለ። ከንዴት ያለው አገር ደረስሁ ብሎ ደብቴ እጅግ አጥብቆ ተገረመ።

ደብቴ መንገዱን ይዞ ወደ ከተማው ሲጓዝ ከመንገድ ዳር ሰውየው ከምድር ላይ ሲንፈራፈር አገኘ። እንደ ታመመ አውቆ አዝኖለት

“ወንድሜ ሆድ ቁርጠት አሞኻልን” ቢለው ሰውየው

“እንግድያው ስልቻ ያለፋል ብለኻልን” ብሎ መለሰለት።

ደብቴ “ተንዴት ያለው አገር ገባሁ ተልጅ ይዞ እስከ አሮጌው ድረስ የቀላጅ አገር ነውሣ” ብሎ መንገዱን ተጓዘ።

እንግዴህ ደብቴን እንተው ወደ ተግባሩ ይሂድ። ደግሞ በሌላ ጊዜ

አቶ አማ የሚባል ሀብታም ጌታ ነበር። እጅግ አጥብቆ ቀልድ ወዳጅ ነበረ። አጋፋሪውም እንደ ጌታው ቀልድ ወዳጅ ነበረ። እንደዚሁ ሁነው ሲኖሩ አንድ ቀን አቶ አማ ጥሩ በቅሎ አስገዛ። አጋፋሪውን አስጠርቶ

“እችን በቅሎ ጫንና መንገድ አሳያት” ብሎ አዘዘው።

“እሺ የኔታ” ብሎ በቅሎዋን ጭኖ ተቀምጦባት ሄደ።

ሁለት መንታ መንገድ ሲደርስ ዱብ ብሎ ወርዶ

“ያውልሽ እንግዴህ። የሸዋ መንገድ ይህ ነው። የጐጃምም መንገድ ይህ ነው። የጐንደርም መንገድ ይህ ነው። የትግሬም መንገድ ይህ ነው። ጌታሽ መንገድ አሳያት ብሎኛልና የወደደሽውን መንገድ ይዘሽ ሂጅ” ብሎ እንደተጫነች ለቀቃትና ወደ ቅልውጡ ውሎ ወደ ማታ ኸጌታው ተመለሰ።

እጅ ተነሳ በኋላ አቶ አማ “ጌታው በል አንተ ለበቅሎዋ መንገድ አሳየኻትን” ብሎ ጠየቀው።

“አዎን የኔታ ያራቱን አገር መንገድ አሳየኋት የወደድሽውን ያዥና ሂጂ ብየ ለቀቅኋት” ብሎ አለ።

ጌትዮም ተናዶ

“መቼም መሽቷልና አድረው በነግህ ተነሱ በቅሏን እንፈልግ” ብሎ አቶ አማ አሽከሮቹንና አጋፋሪውን አዘዘ።

ተነስተው ፍለጋቸውን ያዙ። ሲፈልጉ ሲፈልጉ የበቅሎዋ ድምጥማጥዋ ጠፋ። በመጨረሻ የጣላት አጋፋሪ ያቶ አማ አሽከር አገኛት። ዳሩ ግን ገሚስ ጐንዋን ጅብ ተጋብዟት። ማዘኑን ትቶ መቼም ቀልድ ቤት ያጠፋል፣

“የኔታ በቅሎዋን አገኘኋት። ዳሩ ግን ጅብ በልቷት ጌትዮው አማ” አለ አጋፋሪ። “አላማም አመስግኖ በላ እንጂ”።

ጌትዮ ደርሶ ጥምቧን አይቶ “እንሂድ ኸቤታችን” አለ ተነስተው ኸቤታቸው ገቡ።

ከቤት ገብተው ጥቂት እንደ ቆዩ ዝናብ መጣ። አጋፋሪው ገብቶ ለጌታው

“ዝናብ መጣ” ብሎ ነገረ።

ጌትዮው “ግባ በለው” አለ።

ከቤቱ ላይ ወጥቶ ዝናቡ እንዲገባ ክዳኑን ምንቅርቅሩን አወጣው ለባለቤቱም ከቤት ለገቡትም እንግዶች ሳቅ ሆነ።

አንድ ቀን ካቶ አማ እንግዶች መጡበት። ጋን ጠላ ያልተቀዳ ቀረበ። ቀልደኛ አጋፋሪውን

“እያሸህ ቅዳ” አለው።

እጀጠባቡን ወደ ክንዱ ከፍ አድርጎ እጁን ዘው አግብቶ ጠላውን በጁ ያሸው ጀመረ። አቶ አማ

“ምነው በጅህን ብየኻለሁ?”

“በግሬማ እንግድያው የኔታ ይጠየፋሉ ብየ ነዋ” ብሎ እግሩን ከጋኑ አግብቶ በእግሩ ጠላውን ያሸው ጀመረ።

አቶ አማ ተናደደና “ንሳ ጥፋው” አለ። የሚመታው አጋፋሪ ነበር ቶሎ ፈጥኖ ተነስቶ ደህና አርፎ የቆመውን ልጅ ጆሮ ግንዱን አቀለጠው። አቶ አማ

“እርሱንን ብየኻለሁ?“

አጋፋሪው፦

“እርሰዎንማ እንግዲያው እንዳልጠፋ ጌታየ ነዎ ብየ ብፈራ ነዋ” አለ። በዚህ የተነሳ ብዙ ሳቅና ጨዋታ ሆነ።

አንድ ቀን ደሞ ካቶ አማ እንግዶች መጡበት “ግብር አቅርቡ” አለ። በገበታ በሰደቃ ማዕድ ቀረበ። በሰታቴም ወጡ ቀረበ።

አጋፋሪው ላቶ አማ ባለሟል ነውና ከሁሉም ነገር አለሁ ባይ ነው። ይልቁንም እንግዳ በመጣ ጊዜ ቅድም እንዳልነው ወጡ በቀረበ ጊዜ አቶ አማ

“ወጡን ጠይቀው” አለ።

አጋፋሪ ወደ ወጡ ጥቂት አጐነበሰና ሲያበቃ

“ተየት መጣህ ይሉሃል” አለው።

ወዲያው ቀና ብሎ ለጌታው ሲል “ወጡን ጠየቅሁት ጨው ተወልቃይት፣ በርበሬውና ቅመሙ ተዘጌ መጣሁ ይላል የኔታ” አለ።

ሳቅና ጨዋታ ሆነ።

[ምንጭ] – Major J. Eadie. 1924. “An Amharic Reader”. pp. 39-42

4 thoughts on ““ቀልድ በመንገድ” (ወግ)

አስተያየት ለመስጠት

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s