“እንዳለጌታ ከበደ” (ቃለመጠይቅ)

ቆይታ ከእንዳለጌታ ከበደ ጋር

(ከታኅሣሥ 1998 ዓ.ም እትማችን የተወሰደ)

.

ባለፉት አመታት ከደመቁት የስነጽሑፍ ኮከባት መሀል ወልቂጤ ያፈራችው እንዳለጌታ ከበደ አንዱ ነው። በ”አዲስ አድማስ” ጋዜጣ፣ በ”እፍታ” እና “ክንፋም ህልሞች” መድበሎች ካቀረበው ሥራዎቹ ሌላ በ1996 ዓ.ም “ከጥቁር ሰማይ ሥር” እንዲሁም በ1998 “ዛጎል” የተሰኘ ረጅም ልብወለድን አቅርቦልናል። እንዳለጌታን በ1998 ዓ.ም ከአዲስ አበባ በስልክ አግኝተነው ነበር።

እንዴትወደስነጽሑፍአለምገባህ? ከየትስጀመርክ?

ለመጀመሪያ ጊዜ ግጥም የጻፍኩት ሰባተኛ ክፍል እያለሁ ነው። አንድ ጓደኛችን ግጥም መድረክ ላይ አቀረበ። እና ያኔ ተጨበጨበለት፤ በጣም ሙገሳ በዛለት። እኔ ደግሞ ያቺ ግጥም ከጋዜጣ እንደተወሰደች አውቃለሁና እንዴት ባልሰራው ስራ የኔ ነው እያለ ጉራውን ይቸረችርብናል ብዬ ተናደድኩ። ጓደኞቼ ደግሞ “ታዲያ በዚህ እድሜው ከየት ሊያመጣ ይችላል፤ ከባድ እኮ ነው” ብለው መልሰው እኔን ተቆጡኝ። እኔም ይህን ያህል ከባድ አይደለም ብዬ አንድ ግጥም ጽፌ ለመምህሩ ሰጠሁ። መምህሩ ግን ከድርሰቱ ይልቅ የወደደው እጅ ጽሑፌን ነበር። ቢሆንም አበረታቶኝ ለወላጆች ቀን ዝግጅት አቀረብኩት።

እንዲሁም ቤት የምሰማውን ተረትና ታሪክ ቀይሬ አሻሽዬ ለሰው አወራ ነበር። አሁን ሳስበው ወደ ድርሰት ማዘንበሉ ያኔ የተጀመረ ይመስለኛል። ቤተ ክርስቲያንም አካባቢ እሄድ ስለነበር የቅዱሳን ገድልና ታሪካዊ ነገሮች አነብ ነበር – በተለይ ተስፋ ገብረሥላሴ ዘብሔረ ቡልጋ የሚያሳትሟቸውን። የጸሎት መጽሐፎቹ ግን የዛን የአራተኛ ክፍል ያለሁበትን ምኞቴን አልያዙም ነበር። ያኔ ምኞቴ በትምህርቴ በጣም ጎብዤ አባቴን ማስደሰት ነበር። የጸሎት መጽሐፎቹ ግን የሚሉት ጳጳሱን ባርክ እንዲያ የመሳሰለውን ነው። በልጅነት አእምሮዬ የጳጳሱ መባረክ ጥቅሙ ሰላልገባኝ ትናንሽ የጸሎት መጽሐፎች እጽፍ ጀመር – እኔ መሆን የምፈልገውን ቤተሰቦች ከኔ የሚጠብቁትን። “እግዚአብሔርዬ ከተማሪዎች ሁሉ የተሻለ ውጤት እንዲኖረኝ አባቴም በኔ ደስ እንዲለው አድርግልኝ” እያልኩ እጽፍ ነበር። ከዛም ቀስ በቀስ ወደ ልብወለድ ንባብ ገባሁ።

የትኞቹንየልብወለድጽሑፎችታነብነበር?

መጀመሪያ ያነበብኩት “ሽልንጌን” የሚል አማርኛ መጽሐፋችን ውስጥ የሚገኝ አጭር ልብወለድ ነበር። ከዛም ሳንቲም ሳገኝ – ያኔ መጽሐፎች 3.50 ወይም 4.50 ያወጡ ነበርና – ያገኘሁትን ሳላማርጥ አነብ ነበር። መጀመሪያ በጣም የወደድኩት አጭር ልብወለድ የስብሐት ገብረ እግዚአብሔርን “አምስት ስድስት ሰባት” ነበር። እሱ ግን ታዋቂ መሆኑን ያወቅኩት አስረኛ ክፍል እያለሁ የአማርኛ መምህራችን ከታዋቂ ደራሲዎች አንዱ ስብሐት ነው ብሎ ሲነግረን ነው። ያኔ መምህሩ እኔ የምወደውን ደራሲ ሰላደነቀልኝ በጣም ደስ አለኝ። ቀጥሎም ወደእነ በዓሉ ግርማ …

ያኔበአካባቢህየስነጽሑፍክበብነበር?

እኔ ተወልጄ ያደግኩት ወልቂጤ ነው። እና ያኔ እንኳን ላይብረሪ ይቅርና መጽሐፍ መሸጫ መደብሮች  አልነበሩም። በየስንት ወሩ አንዴ ብቅ የሚል እየዞረ የሚሸጥ አንድ ሰው ነበር። እና ከሱ ነበር መጽሐፍ የምንገዛው። ታዲያ ሰው ቤት ስሄድ የመጀመሪያ ትኩረቴ መደርደሪያዎችን ማየት ነበር። ከዛም ካላነብኳቸው መጽሐፎች አንዱን መርጨ አነብ ነበር። በማንበብ ረሀብ ውስጥ ሰላደግኩ ነው መሰለኝ፣ ቆይ ሳድግ ትንሽም ቢሆን ቤተ መጻሕፍት እከፍታለሁ የሚል ስሜት ነበረኝ። አስራ ሁለተኛ ክፍል ስጨርስም ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም የሚያስገባ ነጥብ አልነበረኝም። እና ያኔ ትንሽዬ ክፍል ውስጥ መጽሐፎቼን አሰባስቤ ማከራየት ጀመርኩ – ለ24 ሰአት 25 ሳንቲም። እዛም ብዙ ሰዎች – ተማሪዎች መምህራን – ይመጣሉ፤ መወያየት ጀመርን። ከዛም “ተስፋ ቡክ ክለብን” ከፈትን፤ የስነጽሑፍ ሰዎችን የሚያበረታታ እንዲሁም የቀለም ተማሪዎችን የሚያግዝ አንዳንድ ስራዎችን መስራት ላይ አተኩረን ነበር።

ወደአዲስአበባእንዴትመጣህ?

መጽሐፍ በማከራየት የሰበሰብኩትን ገንዘብ ይዤ ዕቁብ በመግባት አንድ ሶስት ሺ ብር ሲሞላ ወደ አዲስ አበባ ተጓዝኩ። ፍላጎቴ ስነጽሑፍ መማር ቢሆንም ይህን ዘርፍ የሚያስተምር የግል ተቋም ሰላልነበረ ዩኒቲ ኮሌጅ በመግባት ጆርናሊዝም እና ኮምዩኒኬሽን ተማርኩ።

የመጀመሪያመጽሐፍህስ?

መጀመሪያ ገንዘብ ስሰበስብ መማር ላይ አተኮርኩ። ቀጥሎ ደግሞ ወልቂጤ የነበረውን ስራ ወንድሞቼ ያግዙኝ ነበረ እና ገንዘቡ ሲጠራቀም የኔን ስም የያዘ መጽሐፍ ለማሳተም የነበረኝን ፍላጎት እውን ለማድረግ አሰብኩ። አንዳንድ አጫጭር ልብወለዶቼ ከዚህ በፊት አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ወጥተው ነበር፤ ጓደኞቼ እንዲሁም የማከብራቸው ሰዎች ጥሩ አስተያየት ሰጥተውኝ ነበር። ነገር ግን እነዚህ አጫጭር ልብወለዶች ተሰባስበው አንድ የራሴ የሆነ ቀለም ማሳየት እፈልግ ነበር። እንዴት እንደማስብ ማሳየት እፈልግ ነበር። መጀመሪያ ግጥም ለማሳተም አሰብኩ። ያኔ ግን ብዙ ገጣሚዎች ስራዎቻቸውን ለንባብ ያበቁበት ጊዜ ነበረና አይ አጫጭር ልብወለድ ቢታተም በአመት አንዴ ነውና ለምን የኔዎቹን ሰብስቤ አላሳትማቸውም ብዬ አሰብኩ። ከዚህ በፊት ለንባብ ከበቁትና ከአዳዲሶቹም ጨምሬ አሥራ ስድስቱን አብሬ አሳተምኩ። “ከጥቁር ሰማይ ሥር”ንም ለማሳተም የፈጀብኝ 12 ሺ ብር ነው። ግማሹን ከኔ ግማሹን ተበድሬ።

ምንያህልኮፒአሳተምክ?

ሶስት ሺ። ሰዎች፣ እኔም ጭምር፣ አይሸጥም ብለን ፈርተን ነበር። መጀመሪያ የተበደርኩትን ገንዘብ ካስመለስኩ ጥሩ ይሆናል ብዬ አሰብኩ፤ ከዛም ካልከሰርኩ ጥሩ ነው አልኩ። ቀስ በቀስ ጋዜጦች ሰለመድበሉ መጻፍ ሲጀምሩ እንዲሁም ሰው ሲነጋገርበት ስመለከት አይ ትንሽ እንኳን ማትረፍ ብችል ማለት ጀመርኩ። አሁን መጽሐፉ ከወጣ ሁለት ዓመት አልፎታል። እና ገበያ ላይ አለ ማለት ያስቸግራል። ባለፈው አንድ ሱቅ ውስጥ ሁለት ሶስት አይቼ እራሴ ገዛኋቸው። እና አሁን አብዛኛው ጸሐፊ አንድ ወይም ሁለት ሺ በሚያሳትምበት ጊዜ ሶስት ሺ ማሳተሜ ብዙ ቢመስልም ከሰባ ሚልዮን ህዝብ በላይ ባለበት ሀገር እንዲህ መሆኑ ንባብ በጣም ማሽቆልቆሉን ያሳያል።

ከጥቁርሰማይሥርዋጋውአስርብርነው።ለመሆኑየአከፋፋዮቹድርሻእንዴትነው?

አከፋፋዮቹ 30 ከመቶ ያገኛሉ። የሽፋን ስዕሉንና Layout ለማሰራት፣ ታይፕ ለማስደረግ፣ እንዲሁም ለማሳተም ለእያንዳንዱ መጽሐፍ 4 ብር ወጥቷል። አከፋፋዮቹ ደግሞ 3 ብር ያገኛሉ። እኔ ደግሞ ለሰዎች በነፃ የሰጠሁትን እንዲሁም የተበላሹትን ኮፒዎች አስበህ ከእያንዳንዱ መጽሐፍ 2.80 አገኛለሁ።

በአንድጋዜጣላይምኞትህአንድአገራዊድርሰትበሚልዮንኮፒእንዲታተምመሆኑንገልጸህነበር።እዛለመድረስምንማድረግያስፈልጋል?

ምን መሰለህ! ብዙ ሰዎች መጽሐፍ የሚያነቡት በሌላው ጎትጓችነት ነው። በአሁኑ ሰዓት መጽሐፎች ውድ ናቸውና “ሳንቲሜን አውጥቼ ከገዛሁ በኋላ የፈለኩትን ያህል ደስታ ባላገኝበትስ? ዝም ብሎ እንቶ ፈንቶ ቢሆንስ?” የሚል አስተያየት አለ። አንዳንዶች “ለመሆኑ በአሁኑ ዘመን ጥሩ ደራሲ አለ ወይ?” ይላሉ። እናም በዚህ ጥርጣሬ አይገዛም ማለት ነው። የሰዉን ስሜት ስመለከት መምህሩ አንብቡ ያላቸውን መጽሐፍ ውለው ሳያድሩ ያነባሉ። ምክንያቱም ካላነበቡ የሚጎድልባቸው እንዳለ ሰለሚያውቁ ነው።

ሁለተኛ ደግሞ ያሉን የቤተ መጻሕፍት ቁጥር ብዛታቸው ስንት ነው ብንል መልሱ ያሳዝነናል። መጽሐፍ ሻጮችንም የሚያበረታታ አካል የለንም። ከሚልዮን በላይ ኮፒ ቢታተም ደስ ይለኛል ያልኩት ከምን አንጻር ነው ቢባል? እንግዲህ የህዝቡን ብዛት አስብ! በየጊዜው ደግሞ የመኃይማኑ ቁጥር ቀንሷል ነው የሚባለው። ይህን ህልም እውን ለማድረግ የንባብንና የውይይት ክበቦችን ማብዛት የራሱ አስተዋፅዖ ይኖረዋል። ምክንያቱም ብዙዎቹ ያነቡና የሚያዋራቸው ሰው የለም። የሚያወያያቸው ሰውም የለም። በአሁኑ ሰዓት  የአንባቢው ቁጥር አንሷል ማለት አስቸጋሪ ነው። ሰዉ ወደ ጋዜጣና መጽሔት፣ የዕለት ተዕለት ወደሆነ ኑሮ የሚያተኩሩ ዜናዎችን ለማንበብ ነው የሚረባረበው። መንግሥት በየቀበሌው ካሉት የመዝናኛ ማዕከሎች መሐል የተወሰኑትን ለንባብ አገልግሎት እንዲውሉ ቢያደርግ የአንባብያንን ቁጥር ማብዛት ይቻላል። ምክንያቱም ወመዘክር ወይም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ብትሄድ ሰልፉ ሌላ ነው። እንኳንስ ቁጭ ብለህ ልታነብባቸው ይቅርና ሰው በዝቶባቸው የማይመቹ ቦታዎች ሆነዋል።

ከደራሲው ብዙ የሚጠበቅ አይመስለኝም – ማለት እንዲነበብለት። የውይይትና የንባብ ክበባት ይህንን ነገር ማጉላትና ማራመድ ይችላሉ። በመገናኛ ብዙኃን የጥበባት ፕሮግራምም አዳዲስ መጻሕፍት ሲወጡ በማስተዋወቅ የአንባብያን ቁጥር እንዲበዛ ማድረግ ይቻላል። የቴሌቪዥን ሚዲያ ስናይ የስዕል ኤግዚቢሽን ሲከፈት ሮጠው ያቀርባሉ። ጥሩ ነው ደስ ይላል። ደራሲያን መጽሐፍ በሚያስመርቁበት ሰዓት ግን ብዙ አይመጡም። አንባቢንና ድርሰትን ለማገናኘት የሚያደርጉት ጥረት የደከመ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ። እነዚህ ሁሉ ድክመቶች መቀረፍ ቢችሉ በተወሰነ መንገድ የአንባብያንን ቁጥር ማብዛት እንደሚቻል አስባለሁ።

ሣህለሥላሴ ብርሃነ ማርያም አንድ ዝግጅት ላይ ጥናት አቅርበው በደርግ ዘመን ብዙ አንባቢዎች ነበሩ ብለዋል። ለምሳሌ የሲሳይ ንጉሡ “ሰመመን” 70-80 ሺ ኮፒ ታትሞ ተሽጧል። አሁን ግን ደራሲዎች የሚያሳትሟቸው መጽሐፎች ከ5 ሺ ኮፒ ብዙም ፈቀቅ አይሉም። ለምንድነው? አስበው እንግዲህ የህዝብ ቁጥር ጨምሯል። ነገር ግን የአንባቢያን ቁጥር እየቀነሰ ነው። ያኔ ጎትጓች ነበረው። ያሁኑ ያህል ጋዜጦች አልነበሩም። ሚዲያ አልነበረም፤ ኢንተርኔት ጊዜን አያጣብብም ነበር። ሲኒማዎችም አልተበራከቱም። አቶ ሣህለሥላሴ ሲናገሩ ያኔ ጋዜጦች “ወታደሩ ሰለማያነብ ንቃተ ህሊናው አልዳበረም” እያሉ ይወርፉ ነበር። ወታደሩም እኛ ነን ወይ የማናነበው፤ እኛ ነን ወይ ንቃተ ህሊናችን ያልዳበረው በማለት መጽሐፍ ይገዛ ነበር። ይላክለትም ነበር። በአሁኑ ጊዜ ግን ወታደሩ እንዲያነብ ግፊት ስለሌለው የተወሰነ አንባቢዎችን አጥተናል ሲሉ ሰምቻለሁ።

አንተ፣ በዕውቀቱሥዩምናአማኑኤልመሃሪስትረዳዱይታያል።ከጥቁርሰማይስርውስጥያሉትንስዕሎችየሳለውምበዕውቀቱነው።የደራሲዎችመተባበርናአብሮመስራትንእንዴትታየዋለህ ?

አብሮ መስራት ስራውን የተሸለ ለማድረግ ምንም ጥርጥር በሌለው መልክ ያግዛል። ለምሳሌ በዕውቀቱ “ኗሪ አልባ ጎጆዎች” የሚለውን መጽሐፉን ከማውጣቱ በፊት አንዳንድ ግጥሞቹን እንዲያወጣ መክረነው ሀሳባችንን ተቀብሏል። ይህ ትውልድ ውስጥ መንፈሳዊ የሆነ ስሜት አለ። እርስ በእርስ የመተጋገዝ ነገር አለ። ከሶስተኛው መጽሐፌ ቀደም ብሎ በዕውቀቱ መጽሐፍ ቢያወጣ ደስ ይለኛል። ሙሉ ትኩረታችንንም እዛ ላይ አድርገን ብንሰራም በጣም ደስ ይለኛል። ምክንያቱም እሱ የሚጽፋቸውን ነገሮች እወዳቸዋለሁ። የኔ መጽሐፎችንም ሳሳትም በዕውቀቱ የራሱ የሆነ እገዛዎች ነበሩት፤ አብዛኛዎቹን ሀሳቦቹን ተቀብያቸዋለሁ። ሰለዚህ የምጽፈው ጽሑፍ ወደ ህዝብ እንዲደርስ የራሱ የሆነ አስተዋፅኦ አድርጓል።

በእኛ መሀከል መተጋገዙ ጥሩ ነገር ለህዝብ ለማቅረብ ከመጓጓት ስሜት ነው። ፍቅርህን የምትገልጸው የምትወደውን ነገር የሚወዱ ሰዎች በማብዛት ነው። እኔና ጓደኞቼ ጥበብን እንወዳለን። ኪነትም የተለየ ስሜት ይሰጠናል። በጣም ጥሩ ነገር ስናዘጋጅ እንቀባበላለን። ለምን ይሄ ነገር ጋዜጣ ላይ አይወጣም እንላለን። የህብረት መዝሙር ላይ ከሚሳተፉ ሰዎች መሃል እንደ አንዱ ነን። እያንዳንዱ ዘማሪ የራሱ የሆነ ድምጽ አለው። በሁሉም ባንመሳሰልም አንድ ላይ ስንደረደር ግን እራሱን የቻለ ጥዑመ ዜማ ሊወጣ እንደሚችል እንገምታለን። መተባበራችን እገዛ እንደሚያደርግ እገምታለሁ። ቢያንስ ቅንነትን ለተተኪው ትውልድ ማሳየት ነው።

እናመሰግናለን።

One thought on ““እንዳለጌታ ከበደ” (ቃለመጠይቅ)

አስተያየት ለመስጠት

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s