“ሙሉጌታ አለባቸው” (ቃለመጠይቅ)

“ቆይታ ከሙሉጌታ አለባቸው ጋር”

(ቃለመጠይቅ)

.
[ከአንድምታ ጋር የተደረገ ውይይት]

.

[ሙሉጌታ አለባቸውን በርካቶቻችን የምናውቀው በያዝነው ዓመት ባሳተመው “መሐረቤን ያያችሁ” የተሰኘ የልብወለድ መጽሐፉ ነው። አንዳንዶቻችንም በተወዳጁ “አዲስ አድማስ” ጋዜጣ እና በቀድሞው “አዲስ ጉዳይ” መጽሔት አጭር ልብወለዶቹን እና ትርጉሞቹን አንብበናል። ምናልባት ጥቂቶቻችን ደግሞ “መቅረዝ የኪነጥበብ አፍቃሪያን ማኅበር” ውስጥ አብረነው ተወያይተን ይሆናል።

ሙሉጌታ የመጀመሪያ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በወልዲያ፣ ከፍተኛ ደረጃውን ደግሞ በሀዋሳ እና በአዲስ አበባ ተከታትሏል። በሥራ በኩልም በጋዜጠኝነት፣ በተርጓሚነት፣ በአርታዒነት እና በሕዝብ ግንኙነት ዘርፎች በማገልገል ላይ ይገኛል። በትርፍ ጊዜውም ሥነጽሑፋዊ መጣጥፎችን እና ድርሰቶችን እያቀረበ ነው። አንድምታ ሙሉጌታን በቅርቡ በሥነጽሑፍ ዙርያ አነጋግራው ነበር።]

በቤታችሁ የነበረው የትረካ ንባብ ባህል ምን ይመስል ነበር?

ልጅነቴ በትረካ የተሞላ ነበር። ያሳደገችኝ አደይ ብዬ የምጠራት አያቴ ናት። የእሷን ሩብ ያክል እንኳን መተረክ ብችል እንደ እኔ ያለ ጸሐፊ አይገኝም ነበር። ከተረከችልኝ ውስጥ “የየዋህ ባልና ሚስቶቹን”፣ እንዲሁም “የአያ ድቡልቡሌን” ታሪክ ሳስታውስ አሁን ራሱ ምናቤ በግልፅ በተሳለ ጣፋጭ ትውስታ ይሞላል። አባቴ እና እናቴ ደሞ አስተማሪዎች ነበሩ። አባቴ ጠዋት የእንግሊዝኛ ተረቶች እያነበበ ይተረጉምልኝ ነበር። “The Axe Porridge” አስታውሳለሁ። ርዕሳቸው የጠፋብኝ ሌሎች ብዙ ተረቶችም አሉ። እሱ ጠዋት በእንግሊዝኛ ተረት የከፈተውን ቀኔን ማታ አደይ በአማርኛ ተረት ትዘጋዋለች።

ፊደል መቁጠር ከጀመርኩ በኋላ የመጀመሪያው ሰፊ የንባብ ጊዜዬ የክረምት ወቅት ነበር። በእርግጥ ሁለቱም ወላጆቼ አስተማሪዎች ስለነበሩ ሳልወድ ከዓመት እስከ ዓመት ወረቀት ላይ ማፍጠጥ ነበረብኝ። አንደኛ ደረጃን እስክጨርስ ልክ ሰኔ ላይ ትምህርት እንደተዘጋ የሚቀጥለው ክፍል መጽሐፎች ቤት ድረስ ይመጡልኛል። ከመደበኛ የትምህርት ጥናት ሸፍቼ ልቦለድ እና ታሪክ ንባብ ውስጥ ሳልሠወር በፊት የክረምት ንባቤ ሳይንስ፤ ኅብረተሰብና ስነ-ሕይወት ነበር።

ቆይቶ ግን ከትምህርት ውጪ ያሉ መጽሐፎች ይመጡልኝ ጀመር። አማርኛ መማሪያ መጽሐፎች ውስጥ ያሉትን ታሪኮችም እወዳቸው ስለነበር የሌሎች የክፍል ደረጃዎችን መጽሐፎች እየተዋስኩ አነባለሁ። “መጀመሪያ የመቀመጫዬ ይውጣ” ያለችው ዝንጀሮ ታሪክ በግጥም ሁሉ ነበር። አሁን ድረስ አልረሳውም። መማሪያ መጽሐፎቻችን ውስጥ ከ“ደማሙ ብዕረኛ” (መንግሥቱ ለማ)፣ ከታደሰ ሊበን፣ ከበአሉ ግርማ ሥራዎች የተቀነጨቡ ታሪኮች ነበሩ።

ተወልጄ ያደግኩባት የወልዲያ ከተማ የሕዝብ ቤተ-መጻሕፍት ይመስገንና “ላጠና ነው” በሚል ሰበብ ሄጄ ብዙ አነብ ነበር። ሥራዎቹን በአማርኛ ትርጉም አንብቤ በሼክሲፒር ለመጀመሪያ ጊዜ የተደመምኩት እዚያ ነው። አሁን የዘነጋኋቸውን ግጥሞች ከመጻሕፍት እየገለበጥኩ ቤት ተመልሼ ለአደይ አነብላት ነበር። የኪራይ መጽሐፍትም ነበሩ። የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እያለሁ ሁለት ወር ክረምት ከክፍሌ የምወጣው ሌላ መጽሐፍ ተከራይቼ ለማምጣት ብቻ ነበር ብል ያጋነንኩት ትንሽ ብቻ ነው። በጊዜው መጽሐፍት ማከራያ ቤቱ ውስጥ የነበሩትን ሁሉ አንብቤያቸው ነበር። ሆኖም እንደ አሁኑ መራጭ አንባቢ አልነበርኩም።

እስቲ ስለትምህርት ቤት እና ልጅነት ትውስታዎችህ አካፍለን።  

አምስተኛ ክፍል ስገባ አባቴ እንግሊዝኛ እናቴ ደሞ አማርኛ አስተማሪዎቼ ነበሩ። ያኔ ይሆናል ሳላስበው በቋንቋ የተመሰጥኩት። ከአማርኛ አስተማሪዎቼ የማስታውሰው የአሥራ ሁለተኛ ክፍል አማርኛ አስተማሪዬ ነው። የታዋቂ ሰዎች የሕይወት ታሪክ እንዲያመጣልኝ እየጠየቅኩት በእንግሊዝኛ የሚያመጣልኝን ጽሑፍ እየተረጎምኩ በሚኒሚዲያ አቀርብ ነበር። በቁም ነገር የሚሠራ ትልቁ የክበብ እንቅስቃሴ ውስጥ የገባሁት ግን “ራዕይ” የተባለ የአማተር የስነ-ጽሑፍ እና የጋዜጠኞች ማሕበርን ስቀላቀል ነው። እዚያ ውስጥ ያሉ ሰዎች በጣም ጠንካራ ናቸው። በሳል ከያኒያን ናቸው። እኔ በዕድሜም ትንሽም ነበርኩ። በእውነት ሳስበው በዚያ ዕድሜዬ እነሱ መካከል መገኘት ባይገባኝም እንድገኝ አድርገውኛልና አመሰግናቸዋለሁ። አስበው ዛሬ እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ እንኳን የማይደረገውን ያኔ አንዲት ትንሽ ከተማ ውስጥ ወቅቱን እየጠበቀ የሚወጣ ጋዜጣ ነበረን!

ከእንግሊዝኛ ቋንቋ እና ሥነጽሑፍ ጋር እንዴት ተዋወቅክ?

እንግሊዝኛ አንብቤ መረዳት ስጀምር አባቴ ያነብልኝ የነበረውን የተረት መጽሐፍ በራሴ ማንበብ ጀመርኩ። ከዚያም ወልዲያ የሕዝብ ቤተ መጻሕፍት ሄጄ “Short Story International” የተባለ በተከታታይ የሚወጡ የዘመናዊ ጸሐፊዎችን ሥራዎች የያዙ በርካታ መጻሕፍት አገኘሁ። “The Penguin Book of Very Short Stories” የሚልም ነበረ። ከእነዚህ ጥቂቱን ተርጉሜያቸዋለሁ።

ኮስተር ብዬ ማንበብ የጀመርኩት ግን ዘግይቼ ነው። በሀዋሳ እና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ (አአዩ)። በተለይ በአአዩ ቆይታዬ ሰፊ የማንበቢያ ጊዜ ነበረኝ። ኬኔዲ ቤተ-መጻሕፍት ብዙ መጽሐፎቹ ጠፍተውበት እንኳን ብዙ ሰጥቶኛል። በኋላ ላይ የተወሰኑትን ወደ አማርኛ የተረጎምኳቸውን የጄምስ ጆይስን ሥራዎች፤ ቻርለስ ዲከንስ፤ እና የግሪክ ጸሐፌ ተውኔቶችን ሥራዎች የእነ ሶፎክለስ፣ የእነ አሪስቶፌንስ፣ የሌሎችም። ፈራ ተባ እያልኩ ፍሮይድ እና ያንግን ማንበብ የጀመርኩትም እዚያው ነው። ጸጋዬ ገብረ መድኅን በዋናነት በአማርኛ እንደተጻፉ አድርጎ ያቀረበቸውን የሼክስፒር ተውኔቶች አንብቤ በተአምራዊ ቋንቋው የማለልኩትም በዚህ ጊዜ ነበር።

ዋሳ ኒቨርስቲ ሥነጽሑፍ እንድትማር እን ወሰንክ?

አስቤው አልነበረም። ፍላጎቴ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋዜጠኝነት መማር ነበር። አሁን ሳስበው እዚህ የትምህርት ክፍል ውስጥ ባለመመደቤ ራሴን እንደ ዕድለኛ እቆጥራለሁ። ምክንያቱም የተመደብኩበት የትምህርት ክፍል በዋናነት ሥነ-ጽሑፍ ላይ ቢያተኩርም ከጋዜጠኝነት ጋር ስለሚያያዙ ጉዳዮች ሁሉ በቂ እውቀት ጠቅለል አድርጎ ሰጥቶኛል። ጋዜጠኝነት፣ የሕዝብ ግንኙነት፣ አርትኦት፣ ማስታወቂያ ወዘተ…

ዋሳ ሳለህ “መቅረዝ የኪነጥበብ አፍቃሪያን ማኅበር ውስጥ ምን አይነት እንቅስቃሴ ደረ ነበር?

ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የነበረኝን ቆይታ የማይዘነጋ እንዲሆን ካደረጉልኝ ነገሮች አንዱ መቅረዝ ነው። በየሳምንቱ አንዴ እንገናኝና ሁሉም የጻፈውን ያነባል። ጠንካራ የሂስ ባህል ነበረን። በተማሪነት ዘመኔ እንደዛ ዓይነት ቀጥተኛ እና ክሪቲካል ሂስ መሰጣጠት ለምጄ በኋላ ሰፊው ዓለም ውስጥ ስገባ ግን በተቃራኒው ሆኖብኝ ሁኔታውን ለመረዳት ተቸግሬ ነበር። በአብዛኛው በግል ትውውቅ መረብ እና ካብ ለካብ በመተያየት ደንብ እንደሚዘወር ሲገባኝ እውነታው ይሄ ነው ብዬ ለመቀበል ጥቂት ጊዜ ወስዶብኛል።

መቅረዝ ውስጥ የተመረጡ ሥራዎችን የምናቀርብባቸው ዝግጅቶችም ነበሩን። መቅረዝ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው ባህል ማዕከል አቻ ነበር። አብዛኞቹ አባላቱ በአሁኑ ሰዓት ታዋቂ ጋዜጠኞች፣ ደራሲዎች እና ገጣሚዎች ሆነዋል። ራሳቸውን ቢደብቁም ውብ ግጥሞችና አስደማሚ ትረካዎችን የሚጽፉም አሉ።

ዋሳ ሳለህ የአማርኛ ሥነጽሑፍ ንባብህ በምን መልኩ ተቀየረ? የእንግሊዝኛስ?

አንድ የንባብ ቡድን ነበረን፤ በየወሩ ገንዘብ እያዋጣን በአባላቱ ጥቆማ መሠረት መጽሐፍት ገዝተን እሱን በተራ እናነባለን። በአብዛኛው የአማርኛ መጻሕፍት ነበሩ። በዋናነት ታሪክ እና ስነ-ጽሑፍ። መጻሕፍት ከማገኘትም በላይ ጓደኞቼ ምን ዓይነት መጽሐፍ ማንበብ እንዳለብኝ አቅጣጫ ይሰጡኛል። እንደ በፊቱ በአግበስባሽት ማንበብ አይቀጥልም።

የተማርኩት ትምህርት የእንግሊዝኛ ስነጽሑፍ ውስጥ የትኞቹን ግጥሞች፤ የትኞቹን ልቦለዶች እና የትኞቹን ትያትሮች ማንበብ እንዳለብኝ መንገዱን መርቶኛል። አሁን ድረስ አንብቤ ያልጨረስኩት መለሎ የርዕሶች ዝርዝር አለኝ። የምማረው ትምህርት ራሱ ሥነ-ጽሑፍን ማንበብና መረዳት ስለነበር በደስታ ብዙ አነባለሁ። አንብብ ተብዬ በአስተማሪዎቼ ከታዘዝኩት ዘልዬ ሁሉ የዩኒቨርሲቲው ቤተ-መጻሕፍት የደረደራቸውን መጻሕፍት እገላልጣለሁ። የሄሚንግዌይን A Farewell to Arms እና የቼኑ አቼቤን No Longer at Ease በባዶ ቤተ መጻሕፍት ውስጥ ተቀምጬ ሳነብ አስታውሳለሁ። የጄኬ ሮውሊንግስ መሳጭ ፋንታሲ Harry Potter Seriesን ከአንድ ወዳጄ ጋር እየተሽቀዳደምን ደጋግመን እናነብ ነበር።

የትርጉም ሥራዎችስ በዚህ እድሜህ ወቅት ሞካክረህ ነበር

ትርጉም መስራት የጀመርኩት በ1998 ዓ.ም. ነው። አስራ ሁለተኛ ክፍል ነበርኩ። ለትምህርት ቤታችን ሚኒ ሚዲያ ከማዘጋጀው ውጪ በጊዜው እሳተፍበት በነበረው የሥነ-ጽሑፍ እና የጋዜጠኞች ማሕበር አቀርብ ነበር።  የሕዝብ ቤተ-መጻሕፍት ሄጄ ሙሉውን ታሪክ በእጄ ጽፌ ከገለበጥኩ በኋላ የምተረጉመው ቤቴ ሄጄ ነበር። በእንደዚህ ‘ጥንታዊ’ ዘዴ የሠራኋቸው እንደ “Shoboksh and the Hundred Years” (የግብጽ አገር ልቦለድ) ያሉ አጫጭር ልቦለዶች ነበሩ።

ከዚያ በኋላም ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ደግሞ የስነ ጽሑፍ ኮርሶች ውስጥ መማሪያ ሆነው የሚመጡ ግጥሞችና አጫጭር ልቦለዶችን መተርጎም ደስ ይለኝ ነበር። እነ ጆን ኪትስ፣ ወርድስወርዝ፣ ሼሊ፣ ቴኒሰን እና የሌሎችም ገጣሚያን ሥራዎች። La Bella Dame Sans Merci (“ምሕረት የለሿ ልዣገረድ”) እና Ode to a Nightingale በተለይ አይረሱኝም። ከአጫጭር ልቦለዶችም የልዩ ልዩ አገራት ጸሐፊዎችን ድርሰቶችን እተረጉም ነበር። የእነ ጆቫኒ ቦካሺዮ እና የእነ አንቶን ቼኮቭ። የቼኮቭን “ቫንካ” ተርጉሜ ዶርም ውስጥ ስናነብ አስታውሳለሁ። ከቼኑ አቼቤ አጫጭር ልቦለዶችም እንደዚሁ ለመቅረዝ አቀርብ ነበር።

በአዲስ አበባ ርስቲ የድኅረ ምረቃ የመመረቂያ ጽሑፍህን ርእስ እን መረጥክ?

ርእሴን (Stream of Consciousness) የመረጥኩበት ምክንያት በቴክኒኩ ፍቅር ስለወደቅኩ ነው። ሆኖም አሁን ላይ ሳየው የመመረቂያ ጽሑፌ በኩራት የማቀርበው ሰነድ አይደለም። የሠራሁት አዳም ረታ “እቴሜቴ ሎሚ ሽታ” ላይ ነበር። ብዙ የተመሰጥኩት በመጽሐፉ ቅርጽ ላይ ነበር፤ ይዘቱን ስቼዋለሁ ሁሉ! ከመጀመሪያ ዲግሪዬ የመመረቂያ ጽሑፍ በተቃራኒ፤ የድኅረ ምረቃ ትምህርት የመመረቂያ ጽሑፌ በአሳዛኝ ሁኔታ እንጭጭ የግብር ይውጣ ሥራ ነበር። ለዚህ በዋናነት ተጠያቂው የግል ስንፍናዬ ቢሆንም ዛሬ ላይ ቆሜ ሳየው ግን ሌሎች ምክንያቶችም ነበሩ።

አሁን ዓለም አቀፍ የሥነ-ጽሑፍ ጆርናሎች ላይ የሚወጡ ጽሑፎችን የማየት ዕድል አግኝቻለሁ። መሥፈርታቸው እና የሚፈልጉትን የጥራት ደረጃ ሳይ ‘ከዚህ ቢፊት የሠራሁት ምንድን ነበር?’ የሚል ማወዳደር ውስጥ እገባለሁ። ተማሪዎች ምርጥ የምርምር ጽሑፎችን ማዘጋጀት የማይችሉት የእኛ ሥነ-ጽሑፍ ትምህርት ምን ቢጎድለው ነው? ብዬ እጠይቃለሁ።

ባለፉት ዓመታት ስቡክ ውስጥ ስለተጀመረው የኪነጥበብ ውይይት ምን ትውስታ አለህ?

አአዩ ውስጥ ሳለሁ በፌስቡክ ኪነ ጥበባዊ ውይይቶችን የሚያደርጉ ጥቂት ግለሰቦችን አይቻለሁ። መጀመሪያ ላይ ጠንካራ ሊባሉ ለሚችሉ ሥነ-ጽሑፋዊ ክርክሮች ምቹ ቦታ ነበር። በደራሲዎቻችን ስሞች በተከፈቱ የፌስቡክ ቡድኖች ውስጥ ከብዙ ሰዎች ጋር ብዙ መረጃዎችን የሚለዋወጥ፣ ጠባብ ቢሆንም ጠንካራ እንቅስቃሴ ነበር። አሁን ከስሟል።

የሳይበር ግንኙነት በጊዜ እና በቦታ በተራራቁ ሰዎች መካከል እንዲካሄድ ስለሚያስችል በባሕሪው ኀይለ ቃል መለዋወጥና መዘረጣጠጥን ይፈቅዳል። ሥነ-ጽሑፋችን ውስጥ ከጥንት የነበረውን በግል የትውውቅ መረብ የመደናነቅ/የመነቃቀፍ ልማድም አጉልቶቷል። በቃላት ከተደረተ ጽንፈኛ ትችት በስተቀር ውኃ የሚያነሳ ሀሳብ ይዞ የሚሞግት የሥነ-ጽሑፍ ሂስ እና ውይይት ያነበብኩበት ጊዜ እጅግ ጥቂት ነው።

የጋዜጠኝነት ዘመንህ የሥነጽሑፍ ፍቅርህን አደበዘዘው ወይ አጠነከረው?

ጋዜጠኝነት ሥነ-ጽሑፍን ሊተካልኝ አልቻለም። ተርጓሚነትም እንደዛው። ስለዚህ ሥራዬም እረፍቴም ሥነ-ጽሑፍ ነበር ለማለት አልደፍርም። በጋዜጠኝነት ዋና ሥራዬ መረጃ መሰብሰብና አቀናጅቶ ማሰራጨት ነበር። ጋዜጠኝነት ተጨባጭ መረጃን በማነፍነፍ ተጠምዷል። ስለዚህ ሥነ-ጽሑፍን ሊተካልኝ አይችልም። ከጋዜጠኝነት ደረቅ የመረጃ ስርጭት ለማምለጥ የሚረዱኝ ስልቶች ግን ነበሩ … አንደኛው የመጻሕፍት ዳሰሳዎችን መሥራት ሁለተኛው ደሞ ለሌሎች ጋዜጦችና መጽሔቶች መጻፍ። እነ “አዲስ አድማስ” እና “አዲስ ጉዳይ” ማምለጫ ቀዳዳዎቼ ነበሩ።

ሙሉ ጊዜህን ለሥራ ዓለም ብትሰጥም ባለህ ትርፍ ጊዜ ጥበባዊ ድርሰቶችን እየሰራህ ነው። የእንጀራ እና የጥበብ ነገር እንዴት ነው?

የተለመደ አባባል ልጠቀምና “ጥበብ ጠራችኝ” ብልም የእንጀራ ጥሪ ጎልቶ ይሰማኛል። ምንዳ ስለሚከፈለኝ አይደለም። ጽሑፍን እንደምወደው ሁሉ ሥራንም እወዳለሁ። ስለአንድ ፕሮጄክት ዝርዝር ጉዳይ ተጨንቄ ሥራውን በስኬት ማጠናቀቅ አንድ አጭር ልቦለድ ጽፎ ከመጨረስ የማያንስ ደስታ ይሰጠኛል። በአጭሩ ለሥነ-ጽሑፍ ፍቅር ብዬ የእንጀራ ገመዴን አልበጥስም ማለት ነው።

የስብሐት እና የበአሉ ግር ሥራዎች በአንተ ውስጥ ስለተዉት አሻራ የምትለው አለ?

የስብሐት እና የበአሉን ሥራዎች በጣም እወዳለሁ። ከስብሐት ሥራዎች በተለይ “አምስት ስድስት ሰባት” አንጀቴን ያርሰኛል። ፋንታሲው ጠቅልሎ ወደ ሌላ ዓለም ይወስደኛል። ሁልጊዜም ሲጽፍ ሕይወትን ነው። በአሉም እንደዛው። በተለይ “ከአድማስ ባሻገር” ልብ ላይ የሚደርስ ሥራ ነው። ደሞ በሌላ መጽሐፉ ውስጥ ያቺ ውብ የበአሉ ግጥም አለች!

“የኔ ውብ ከተማ የኔ ውብ አገር

የሰው ልጅ ልብ ነው፤

የሌለው ዳርቻ፣ የሌለው ድንበር!”

ከልብወለድ እኩል የግጥም ፍቅር ያለህ ይመስላል።

ቃላትን ወድጄ የግጥም ፍቅር ባይኖረኝ ግዙፍ ምጸት ይሆን ነበር። ሆን ተብለው በተመረጡ ቃላት የተዋቀረች አንዲት ስንኝ ካነበብኩ መጽሐፉን ዘግቼ በሀሳብ ጭልጥ እላለሁ። ግነት አይደለም። አንዳንዱ ቀኔ ጠዋት አንብቤው በምወጣው ነገር ይወሰናልና ምን ማንበብ እንዳለብኝ እጠነቀቃለሁ። እንደ ዮሐንስ አድማሱ “እስኪ ተጠየቁ” ዓይነት ነገር በጠዋት ካነበብኩ ቀኑን ሙሉ ተረብሼ እውላለሁ።

“አዋሽ ማዶ አብረን እንውረድ” ሲል ጸጋዬ፣ ወይም ገብረክርስቶስ “የፍቅር ሰላምታ” ሲል ፍቅር ካልተሰማኝ ቃላት መውደዴን መጠራጠር መጀመር አለብኝ። የደበበንም “ጊዜ በረርክ በረርክ” ሳነብ ልቤን ካልነዘረው። በእውቀቱ ደግሞ ድንቁን ሀሳብ በውብ ቋንቋ አሽሞንሙኖ በልዩ የስንኝ ምጣኔው ሲያስቀምጥ ካልተገረምኩ “በድንቅ አብቃይ ምድር” ሳይገርመኝ እየኖርኩ የማልፍ ትውልድ ሆንኩ ማለት ነው።

እንደመታደል ሆኖ የአማርኛ ሥነ-ጽሑፍ በዝርው ከሚያቀርብልኝ አማራጮች በላይ በሥነ-ግጥም ሰጥቶኛል። ከምወዳቸው ደራሲያን ቁጥር የምወዳቸው ገጣሚያን ቁጥር ይበልጣል።  ደበበ ሰይፉ፣ ነቢይ መኮንን፣ ጸጋዬ ገብረመድኅን፣ ሙሉጌታ ተስፋዬ፣ ዮሐንስ አድማሱ፣ ገብረክርስቶስ ደስታ፣ መንግሥቱ ለማ፣ ሰለሞን ዴሬሳ፣ በዕውቀቱ ሥዩም፣ ጌትነት እንየው፣ የሻው ተሰማ፣ ቴዎድሮስ ፀጋዬ … መአት ናቸው። በመጽሐፍ መልክ ባይሆንም እንኳን የዘፈን ግጥም አለልኝ። በብዛት አለመገኘቱ እንጂ ዝርው ግጥምም አለ!

ከአዳም ረታ ሥራዎች ጋር ስለተዋወቅክበት ኔታ እስቲ ትውስታህን ብታጋራን

በ2000 ዓ.ም ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ማደሪያ ክፍላችን ውስጥ በሚገኘው ሎከር ከተደረደሩት መጻሕፍት መካከል አንድ ወፈር ያለ “ግራጫ ቃጭሎች” የተሰኘ ልቦለድ መዝዤ ማንበብ ስጀምር እንደ ቅዱስ መጽሐፍ ሁሉም ቦታ ይዤው የምዞረው ጥራዝ ይሆናል ብዬ አልጠረጠርኩም ነበር።

የቅርጽ እና የይዘት ድንቅ ውሕደቱ ምን ጊዜም አይጠገብም። ከእንጀራ የተቀዳው ቅርጹ ልቦለዱን ከዓይን እስከ ሰበከቱ እየደጋገምኩ እንድበላው/እንዳነበው ያደርገኛል። በገጸ ባሕሪያቱ ተደንቄ ሳልጨርስ በጣፋጭ ቋንቋው እገረማለሁ። ጎልቶ በማይታይ ሤራ መሳጭ ልቦለድ እንደሚጻፍ ሌላ ማሳያ ነው። ይሄው እስከ ዛሬ ድረስ ዋና ገጸ ባሕሪው መዝገቡ ሥጋ እንደለበሰ ሰው እንጂ በመጽሐፍ ገጾች መካከል እንደሚገኝ ምናብ ብቻ አልቆጥረውም።

ግራጫ ቃጭሎችን ደግሜ ባነበብኩት ቁጥር ከዚህ በፊት ያላየሁት ነገር አገኛለሁ። በጥቅሉ በአማርኛ ቋንቋ እንደዚህ ሊታሰብ እና ሊጻፍ መቻሉ አስደመመኝ።

እጅህ ላይ ስላሉት ድርሰቶች እና ውጥኖች ጥቂት ብትነግረንስ?

የአጫጭር ልቦለድ ቢጋሮች አሉኝ። ሆኖም አሁን ትኩረቴ እሱ ላይ አይደለም። አምርሬ ከመጀመሬ በፊት ማንበብ አለብኝ። ከልቦለድ ውጪ ግን የጀማመርኳቸው ሥራዎች አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል አንድ ልዩ መጽሐፍ አለበት – ለአማርኛ ሥነ-ጽሑፍ ያልተለመደ ዓይነት መዝገበ ቃላት ነው። በቅርቡ ይታተማል ብዬ ተስፋ አለኝ …

ለቆይታው እናመሰግናለን።

 እኔም አመሰግናለሁ።

.

ሙሉጌታ አለባቸው

(ቆይታ ከአንድምታ ጋር)

ሐምሌ 2009 ዓ.ም

.

One thought on ““ሙሉጌታ አለባቸው” (ቃለመጠይቅ)

  1. መጻሓፉን በቆምኩበት ሁላ እያነበብኩ ፈጀሁት።
    እንደዚህ እንደምወደው ባውቅ ሻጩ ፡ባለመነኝ ።. ውድድ ያረኩት። ነው ። ሁሉንም ነገር ።
    ይበል ብዕርህ ይባረክ አይንጠፍ ።

    Like

አስተያየት ለመስጠት

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s