“ያጼ ዳዊት ጀብዱ”
በደብተራ ኀይሉና በሐጅ አሊ
(1800 ዓ.ም)
.
ክፍል አንድ
.
አጼ ዳዊት በነገሡ ጊዜ ግብጽ ያለው የስጥንቡል ንጉሥ፣
“ትገብር እንደሆን ገብር አትገብር እንደሆን አታመልጠኝም ቻለኝ መጣሁ” አለና ላከብዎ … በአጼ ዳዊት።
እርስዎም “ብትመጣ ጦር አለኝና እችልሃለሁ” ብለው ላኩበት።
እርሱም ሳይነሳ የኢትዮጵያን ውሀ ሁሉ በኖራ መልሰው አድርቀው ወደ ምሥራቅ ሰደዱትና ውሀ አጡ ግብጻውያን ሁሉ። ከዚህ ወዲያ ማረኝ ሲል ላከ።
“መማለጃኸንም በ፼ ግመልና በቅሎ አኽያ የተጫነ ወርቅ ብርና ግምጃ ተቀበለኝ። በውሀ ጥም አንለቅ። ግዱን በፈጠረህ አምላክ ማረኝ” ብሎ ላከ።
እርስዎም ሲልኩ፣
“ማረኝስ ታልኸኝ ብር ወርቅ ግምጃ ምን ይሆነኝ? መማለጃየንስ ጌታዬ የተሰቀለበትን ግማደ መስቀል እቃውን ሁሉ፣ የሰማዕታትን ዓጽም፣ ስዕርተ ሐናን፣ የሙሴን ጎሞር ከነጎፍላው፣ የዮሐንስን መስቀል፣ ሉቃስ ወንጌላዊ የሳላቸውን ስዕል፣ የቀራንዮን መሬት ከሊቀ ጳጳሱ ዘንድ ልከህ አስመጣልኝ። እንታረቅ ውሀውንም ልመልስልህ። ይህ ሁሉ ያልሁህ ታልገባልኝ ውሀውንም አልመልሰልህም” ብለው ላኩ።
እርሱም ሉል አደረገና የግብር መዠመርያ ግማደ መስቀሉን፣ ኵርዓተ ርእሱን፣ የተገረፈበትን አለንጋ፣ ራሱን የተመታበትን ብትር፣ ከለሜዳውን፣ ሐሞት የጠጣበትን ቢናግሬ፣ እግሩን እጁን የተቸነከረበትን፣ የቀራንዮን መሬት ደሙ የፈሰሰበትን ጭነው። የቅዱስ ጊዮርጊስን አጽምን፣ የፈረሱን ጭራ ቢሰፍሩት ፵፪ ክንድ ሆነ። የ፳፭ አጽመ ሰማዕታት፣ ስእርተ ሐናን፣ ዮሐንስ ያጠመቀበትን መስቀል፣ ሉቃስ ወንጌላዊ የሳላቸውን ስእላት፣ የሙሴን ጎሞር ከነጎፍላው፣ ከዚኽም የሚበዛ ብዙ እቃ ሰደደልዎና ታረቁ።
ውሀንም መልሰው ሰደዱላቸው። ስለዚህ ኢየሩሳሌምን ግብጽንም አስገበሩት።
ከዚያ ወዲያ የዘንዶ ንጉሥ አለ ቢሏቸው ሠራዊታቸውን ክተት አሉና ዘመቱ እዋጋለሁ ብለው። ዘንዶም አፉን ይከፍትና ፼ ዝሆን እየገባ ሲከማች ጊዜ አፉን ይገጥመዋል። በዚህ ይኖር ነበር። ያን ጊዜ ቢደርሱ አፉን ለቆ አገኙት። ዋሻ አገኘነ ብለው ንጉሥ ከለሠራዊታቸው ገቡ።
ሲገቡ ነፍጥ ቢያስተፉ ፪ ዛሮች ተከሠቱ።
“የዘንዶ ንጉሥ አሉ ይላሉ ወዴት?” ብለው ጠየቋቸው።
“ይህ የገባችሁበት አይዶለውም” አሏቸው።
ንጉሥ ደንግጸው ከለሠራዊትዎ ወጡ። ከዝያ ወዲያ ፰ ቀን በመድፍና በነፍጥ ቢደበድቡት አልላወስ አልቀሳቀስ ብሎ በግድ ሞተ።
ከዝያ በኋላ ምሥራቅ ምድር ሔዱ … ከፀሐይ ጋር እዋጋለሁ ብለው። ለንጉሥ የ፰ ቀን ጐዳና ሲቀረዎ ፊታውራሪው አጠገቧ ሲደርስ፣ እርሷም ከመስኮቷ ስትወጣ፣ ያነን የሰፈውን ፊታውራሪ ሠራዊት እንደ ሰም አቅልጣ ፈጀችው … ንጉሥ ሳይደርሱ።
ከዝያ በኋላ አንድስ የሚሉት አውሬ ከገደል ስር የሚኖር አለ አሏቸው … ሊዋጉ ሔዱ። የ፰ ቀን መንገድ ሲቀረዎ ፊታውራሪው ከገደሉ አፋፍ ሲደርስ፣ ገና ሳይወጣ ድምጡን ቢሰሙ፣ ግማቱ ቢሸታቸው ፊታውራሪው ከለሠራዊቱ አለቀ።
‘አንድስ አንድስ ይሸታል’ የሚሉት ከዚህ የተነሣ ነው።
ደብተራ ኀይሉ እና ሐጅ አሊ
1800 ዓ.ም
.
[ምንጭ] – Bibliothèque Nationale። Eth Ms 144። ቅጠል 18-19።
በጣም ደስ ይላል እስኪ አባካችሁ ቀጥሉ፤
LikeLike