“ሌቱም አይነጋልኝ” (ልብወለድ)

“ሌቱም አይነጋልኝ”

በስብሐት ገብረ እግዚአብሔር

.

.

ምዕራፍ 3

(ገድለ ጥላሁን)

“አያ በለው በለው

አያ በለው በለው

አያ በለው በለው”

.

ታዲያ ዓይናችን አገልጋያችን ነው ትለኛለህ? አገልጋያችን ከሆነ ለምን ትርሲትን ፈልግ ስለው ሄዶ ኃይለሚካኤል ላይ ያርፋል?

ኃይለሚካኤል አንድ የውቤ በረሃ ጀግና ነው። ሰውነቱ ግዙፍ፣ መልኩ ቀይ፣ አፍንጫው ደፍጣጣ፣ ፀጉሩ በጣም ሉጫና በቅባት የሚያብለጨልጭ፣ በጡንቻው የታወቀ ነው። አሁንም ሳየው ሮዛን እጇን ጠምዞ የቀልድ እያስመሰለ ቂጧን በጥፊ ይመታታል። ሮዛ እንዳትስቅ አመማት፣ እንዳታመር የባሰውን እንዳይደበድባት ፈራች። ስለዚህ በውሸት ሳቅና በእውነት ንዴት መሃል፣

“ጋሼ ኃይልዬ! እባክህን ተወኝ ያማል!” ትላለች።

አልተዋትም። ውቤ በረሀ የሚመጣው ሴቶቹን ለመደብደብ ወይም ወንዶቹን ለመገላመጥ ነው።

አንድ ማታ ለምሳሌ ከአንድ ፈረንጅ ጋር ዝናሽ ቤት መጣ። ይኼ ፈረንጅ ፀሐይን ሁለት ውስኪ ጋበዛትና እንሂድ አላት። ሰው አለኝ አለችው። ኃይለሚካኤል ታዲያ ብድግ አለና፣

“የኔን እንግዳ? አንቺ ቂንጥራም!”

እያለ በጥፊ – በእርግጫ – በክርን – በጡጫ ሲያጣድፋት ጊዜ አፍንጫዋ ደማ፣ ዐይኗ አበጠ። አምስት ቀን ተኛች ስትተነፍስ ጎኗን እያመማት ብዙ ተሰቃየች። እስከ ዛሬ በደንብ አልዳነችም፤ ስትስል ወይም ስትስቅ ጎኗን ያማታል። የኃይለሚካኤል ጡንቻ ነው።

ተኝታ ሳለ ልጠይቃት ገብቼ ስናወራ፣

“ለምን አትከሺውም?” አልኳት።

“አንተ ደሞ! ከመቼ ወዲህ ነው ሸርሙጣ ተረገጥኩ ብሎ ‘ሚከሰው?” አለችና ማልቀስ ጀመረች። “ደሞ ብከሰውም እኔ ነኝ ምታሰረው። ወንድሙ የፖሊስ ሻለቃ ነው።”

ኃይለሚካኤል ሲያጠቃ ሴቶችን ብቻ አይደለም። ወንዶችንም ነው። አሀዝ ሲነግረኝ (አሀዝም ራሱ ጉልበተኛ ነው – ብቻ ሴቶቹን አይነካም) አንድ ማታ ሁለቱም አብረው መርካቶ ሾፌሮች ቡና ቤት ገቡ። እዚያ አንድ ጠብዚራ ክብር ዘበኛ ነበር። ስክር ብሎ መጠጥ መቅጃው ባንኮኒ ዘንድ ቆሞ ስለኮርያ ዘመቻ – ስለቶኪዮ ይለፈልፋል። ኃይለሚካእል አሀዝን፣

“አቦ ይኼ ቡፋ ምን ጡሩንባውን ይነፋብናል?” አለው።

“ካማረህ ዝም አታሰኘውም?” አለ አሀዝ።

ኃይለሚካኤል “ተመልከት እንግዲህ” አለውና ጮክ ብሎ፣

“አቦ እዚህ ጩኸት በዛ!” አለ።

ክብር ዘበኛው “ታዲያ ጆሮህን  አትዘጋም?” አለው። ኃይለሚካኤል “አንተ አፍህን አትዘጋም?” አለና እጆቹን ጨብጦ ቀረብ አለው።

“ጆሮሽን ነው በጥፊ ብዬ ‘ምደፍንልሽ”

ኃይለሚካኤል ጠጋ ብሎ ፊቱን ለጥፊ አመቻችቶ ሰጠውና፣

“እስቲ?” አለው።

ክብር ዘበኛው “እንቺ!” አለና አንዴ በጥፊ ወለወለው። ኃይለሚካኤል ፊቱን እያሻሸ፣

“ታዲያ ይኼ የሚገባ ነገር ነው?” አለውና፣ ወንበር ፈልጎ ለብቻው ቁጭ አለ።

አሀዝን አኮረፈው።

ታዲያ ቅድም እንዳልኩት፣ ማሚት እሹሩሩ ቤት ውስጥ ኃይለሚካኤል ሮዛን የቀልድ ሲያጎሳቁላት ከቆየ በኋላ፣ ድንገት እርግፍ አድርጎ ተዋትና፣ ሰዎች መሀል መንገድ እየከፈተ ወደ በሩ በኩል ሄዶ ጥላሁንን ጨበጠው።

ጥላሁን በውቤ በረሀ የታወቀ ረብሸኛ እንደመሆኑ መጠን፣ ልክ ሲገባ እንዳየኸው ሄደህ ካልጨበጥከውና “እንደምነህ ጥላሁን? የት ጠፋህ ባክህን?” ካልልከው ኮራህ ብሎ ይቀየምሃል፤ ትንሽ የጠጣ ጊዜ ነገር ይፈልጋሃል።

ሱሪውን በክንዶቹ ከጎንና ጎኑ ከፍ እያደረገ፣ መፋቂያውን አፉ ውስጥ ከግራ ወደ ቀኝ እያዘዋወረ፣ ደም የለበሱ ትልልቅ ዓይኖቹን እያፈጠጠ፣ በሚያስፈራ ድምጽ “ፈረሰኛውን!” እያለ ይመጣብሃል።

ስለዚህ ኃይለሚካኤልና ሌሎችም የበረሀ ጀግኖች መጥተው ጨበጡት፣ አንገቱን አቀፉት፣ ጀርባውን መታ አደረጉት። በውቤ በረሀ ሥነ ሥርዓት ገበሩለት። አሁን ከኃይለሚካኤል ጋር አብረው እየተሽቆጠቆጡ ጥላሁንን ሰላምታ የሰጡት ጀግኖች፣ ምናልባት ከጥቂት ደቂቃ በፊት ኃይለሚካኤልን ራሱን እየተሽቆጠቆጡ ሰላምታ ሰጥተውታል …

ውቤ በረሀ እንዲያው መጥቶ ደንሶ ገንዘብ ከፍሎ ሴት ተኝቶ የሚኬድበት ቦታ አይደለም። ወንዶች የተሰበሰቡበት ማንኛውም ቦታ ውስጥ አንዱ ከሁሉም መብለጡ መታወቅ አለበት። ከብቶችም መሀል፣ ውሾችም፣ ሰዎችም መሀል፣ አብዛኛው በማህበር የሚኖር ፍጡር መሀል እንደዚህ ነው። የተፈጥሮ ሕግ ሳይሆን አይቀርም። በዶሮ፣ በዝንጀሮና በሌሎችም አንዳንድ ፍጥረቶች መሀል ይህ ህግ ከመጠን በላይ ይሠራል።

አንድ ወንድ ከሌሎቹ ሁሉ በላይ መሆኑ እንዳይበቃው፣ ሌሎቹን ሁሉ ወንዶች ልጅነታቸውን ጨርሰው ሴቶቹን ማሽተት ሲጀምሩ ቢገድላቸው ይፈቅዳል። አንዳንዱማ በሕፃንነታቸው ይገድላቸዋል። እናቶቻቸው አንዳንዶቹን እንደ ሙሴ ደብቀው ያሳድጓቸዋል። ሲያድጉ መጥተው አውራውን ገድለው (አሁን ሸምግሏል) ቦታውን ይወስዳሉ። ተራቸውን እስኪገደሉ ድረስ ይነግሳሉ።

ለምንድን ነው? ያልክ እንደሆነ፣ ለሴቶቹ ነው። ‘እኔ ግን ለሴቶቹ ብዬ አይደለም፣ ለወንድነቱ ነው’ ትላለህ። ራስህን አታለልክ። ወንድ ስትል ከጎኑ ሴት ውስጠ ታዋቂ ነው። ስለዚህ ስማ፣ ውቤ በረሀ መጥተህ ስትጣላ ስትደባደብ የፍጥረትን ህግ መከተለህ ነው። በህጉ መሠረት እንዳሸናፊትህ መጠን ሴትህን ወይም ሴቶችህን ትመርጣለህ። ካንተ ቀጥሎ ከሌሎቹ የሚበልጠው ከቀሩት ሴቶች ውስጥ ይመርጣል።

መጨረሻ የቀረው ወንድ መጨረሻ ይመርጣል፣ ወይም የቀረችውን አንዲት ይወስዳል፣ ምንም ሴት ካልተረፈ ቀረበት። ምናልባት አንተን ተደብቆ ይከተለህና ሴትህን ከጠገብካት በኋላ ለጥቂት ጊዜ ትተሃት አደን ስትሄድ በስርቆሽ ይተኛታል። ግን ዘርህን ቀድመኸው ዘርተሃልና የሚወለደው ልጅ ያንተ ነው፣ ጉልበት የሌለው ዘር ሳይተው ይሞታል። ይህ የፍጥረት ህግ ነው። ብርቱውን ማባዛት፣ ደካማውን ማጥፋት። ክርስቶስም ብሎታል “ላለው ይጨመርለታል፣ የሌለው ግን ያ ያለውም ይወሰድበታል”።

የሰው ስልጣኔ ይህን የጉልበት ህግ ጥሶታል። ግን ላይ ላዩን ነው እንጂ ውስጥ ውስጡን ይህ ህግ አሁንም ይሰራል። እዚህ በረሀ ውስጥ ብታስተውል ጉልበተኛው ነው የፈለጋትን ሴት የሚያገኝ። አንዳንዴ ባለ ገንዘቡ ነው። ለምን? ህገ-ወጥ የሆነው የሰው ስልጣኔ በጉልበትህ እንዳትጠቀምበት ይከለክልሃል። ግን አሁንም ላይ ላዩን ነው እንጂ ውስጡን ብትመለከት እንዴት ነው? ገንዘቡ ከጉልበትህ የበለጠ ጉልበት ነው። የሚገዛውን ጠበቃ፣ የሚያስከትለውን እስራት አስብ – ይኼ ጉልበት አይደለም?

አንድ ማታ ማሚት እሹሩሩ ቤት እኔ፣ ክንፈ፣ አሥራት ዕንቁ እና ጥላሁን ባንኮኒው ዙሪያ ቆመን ስናወራ፣ ጥላሁን እየሳቀ፣

“ለመሆኑ ለምንድን ነው እዚህ በረሀ ጥል የሚበዛው?”

ብሎ ጠየቀና፣ ይህን የፍጥረት ህግ ከዘበዘብኩለት በኋላ፣ በቁጣ ዓይነት ድምፅ፣

“እንግድያው አንተ ለምን እንደ ህጉ መሠረት አትደባደብም?” አለኝ።

 እየሳቅኩ፣

“እኔ ወንድ መቼ ሆንኩ?” አልኩት።

ሌሎቹም ከኔ ጋር ሳቁ። ጥላሁን ግን አፈጠጠብኝ። ስሜት ይጎድልሃል፣ ሰው አይደለህም ብሎ ሁልጊዜ እንደነቀፈኝ ነው። አሁን ግን የተቀየመኝ ከልቡ የጠየቀኝን ጥያቄ ወደ ቀልድ ስላዞርኩበት ነው።

ወደ መደነሻው ወለል እየተመለከተ፣ አፉ ውስጥ መፋቂያውን ከግራ ወደ ቀኝ እያዛወረ፣

“ትርሲትንና ብርሃኑ ተመልከት” አለኝ።

ሁላችንም አየናቸው። ጥብቅ ብለው ተቃቅፈው ታንጎ ይደንሳሉ። የሱ ፀጉር (ከአባቶቹ የወረሰው ረዥም ሉጫ ፀጉር) ከግንባሩ በኩል ወድቆ ከሷ ፀጉር ጋር ተደባልቋል።

“ብርሃኑ እንደምታየው ኮሳሳ ቢጤ ነው” አለ ጥላሁን … “በጉልበትም ቢሆን እዚህ የሚመጡት ወንዶች ብዙዎቹ ያሸንፉታል። በገንዘብም ቢሆን ብዙዎቹ ይበልጡታል። ግን ማንም ቢሆን ትርሲትን ሊወስድበት አይችልም። እውነቴን ነው? You agree?”

“አዎን”

“ታዲያ የዳርዊን Natural Law የምትለው የታል የሚሠራው?”

ረታሁ ብሎ ደስ ብሎታል። በቆንጆ ነጭ ጥርሶቹ ፈገግታ አሳየኝ።

“እንድያውም እዚህ ላይ ነው በግልጽ የሚሠራው” አልኩት።

“እንዴት?”

“እዚህ ቤት ከሚመጡት ወንዶች ሁሉ ከእያንዳንዳቸው ጋር ቢመዛዘን፣ የብርሃኑ ወንድነት እጥፍ ወይም አስር እጅ ነው”

“ኤድ !” አለኝ።

‘የማነህ ቀርፋፋ?!’ እንደማለት ያህል “ድ” ላይ ድምፁን ጫን ብሎ ጎተተው። ሌሎቹ ደስ ብሏቸው ዝም ብለው ያዳምጣሉ። ጥላሁን መጨረሻ ላይ እንደሚቆጣኝ ያውቃሉ።

“አስብ እንግዲህ” አልኩት … “ከብርሃኑ ሌላ ማን ወንድ ነው ደፍሮ ሸርሙጣ ይዞ ፒያሳ መሀል የሚንሸራሸር? ማነው በየቡና ቤቱ ይዟት የሚገባ? ሌሎቻችን እንዲያው እዚህ ስንሆን ቂጣቸውን እየላስን፣ ውጪ ስናገኛቸው እንደማናውቃቸው እናልፋቸዋለን። ማን ነው ሸርሙጣ ወዳጁ ስትታመም ራሱ በቀን ውቤ በረሀ መጥቶ ሀኪም ቤት የሚወስዳት? ገንዘብ መክፈሉንስ ምናልባት የሚከፍል አይጠፋም እንበል። ማነው በየቀኑ እየሄደ አብሯት የሚውል? ማነው የአስታማሚ ፈቃድ አስወጥቶ አልጋዋ አጠገብ ወንበር ላይ ቁጭ ብሎ የሚያድር?”

“ከብርሃኑ ሌላ ማን ጎበዝ ነው ፓርቲ በተደረገ ቁጥር ያችኑ ሸርሙጣ ይዞ ሄዶ ልክ እንደ ልጃገረድ የሚያከብራት? ደሞ ‘ይህን የሚያደርገው ትርሲት ልዩ ስለሆነች ነው፤ በየሄደችበት እንደ ሸርሙጣ ሳይሆን እንደ ጨዋ ሴት ስለምትሆንለት ነው’ እንዳትለኝ፣ እንደ ሸርሙጣ መሆን ትታ እንደ ሴት ወይዘሮ የምትሆንበት ምክንያት ብርሃኑ ሸርሙጣነቷን ስለሚያስረሳት ነው። ሽርሙጥናን እንደ እድፍ ወይም እንደ ብረት ልብስ ብንቆጥረው፣ ካንዲት ሸርሙጣ ላይ እድፏን ለማጠብ ወይም የብረት ልብሱን ቀድዶ ለመጣል ምን ያህል ወንድነት የሚጠይቅ ይመስልሃል? ታውቃለህ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲተኛት ገንዘብ አልከፈላትም። እስካሁንም ቢሆን ሊተኛት ሲል ወይም ከተኛት በኋላ ገንዘብ ሰጥቷት አያውቅም።”

ጥላሁን “ኧረ ባክህን?” አለኝ። አሁን ክርክራችንን ረስቷል። የትርሲትና የብርሃኑ ነገር ደግ ቅን ልቡን ነክቶታል።

“በፍጹም ከፍሏት አያውቅም” አልኩት … “ልብስ ሲያስፈልጋት – ሲያምራት ማለቴ – የጨርቁንና የሰፊውን ዋጋ ትነግረዋለች። ይሰጣታል። አስተውል፣ የፍቅር ስጦታ ነው እንጂ የእምስ ዋጋ አይደለም። አንዳንዴ ለምን እንደሚጨቃጨቁ ልንገርህ? እሱ ገንዘብ ሲሰጣት እሷ አልፈልግም ስለምትለው ነው። ወይም ትንሽ ወስዳ ከዛ በላይ አያስፈልገኝም ስትለው። ለምሳሌ ለፀጉር መሠሪያ ስትጠይቀው አስር ብር ነው ‘ሚሰጣት። እሷ አምስት ብር ይበቃኛል ትለዋለች። ወረፋ ስትጠብቂ ኬክና ጀላቲ ያስፈልግሻል ይላታል። እንግድያው ስድስት ብር ይበቃኛል ትለዋለች። እንግዲህ አትጨቅጭቂኝ ይልና አስቱን ብር በግድ ይሰጣታል።

ትርሲትና ብርሃኑ ዳንሳቸውን አብቅተው አንድ ሶፋ ላይ ተቃቅፈው ቁጭ ብለው እየተሳሳቁ ያወራሉ። ጥላሁን እንደ እናት ደስታና ፍቅር በሞላው ገጽ ይመለከታቸዋል። እኔ ዝም ስል ጊዜ ክርክራችንን አስታወሰና፣

“መጀመሪያ’ኮ ወንድነት አላልክም ጉልበት ነው ያልከው” አለኝ።

“ጉልበትስ ቢሆን ጥላሁን? እንደዚህ ተመልከተው እስቲ? አሁን አንድ ጉልበተኛ ጠብዚራ መጥቶ በጥፊ ብሎት ትርሲትን ቢቀማው አንተ ዝም ብለህ ታያለህ?” አልኩት።

ሱሪውን በሁለት ክንዶቹ ከፍ እያደረገና የወይራ መፋቂያውን አፉ ውስጥ ከግራ ወደ ቀኝ እያዛወረ “አይሆንም!” አለ። ለጠብ ሲዘጋጅ ነው። በሳቃችን መሀል፣

“ይኸውልህ፣ ብርሃኑ የራሱ ጉልበትና ያንተ ጉልበት አንድ ላይ አለው ማለት ነው። የሌሎችም” አልኩት።

“እኔ ምልክ፣ የነዚህ ልጆች ፍቅር እውነተኛ ፍቅር ነው በለኛ” አለ።

“እንዲህ አይምሰልህ!” አልኩና ለምሳሌ ያህል የሚከተለውን አጫወትኩት።

አንድ ሰኞ ማታ ወደ ሁለት ሰዓት ላይ ወንዶች ገና መምጣት ስላልጀመሩ ቤቱ ባዳውን ነበር። ብርሃኑ እዚያ ጥግ ሶፋ ላይ ብቻውን ቁጭ ብሎ ሲጋራ ያጨሳል። እዚህ ጋ ትርሲት፣ ከበቡሽ፣ አስቴር፣ ሦስቱ ካንድ ሰውዬ ጋር ቁጭ ብለው ስለ በረሀ ፍቅር ያወራሉ። (ሌላ ማንም ሰው የለም፣ ሌሎቹ ሴቶች እውስጥ እራታቸውን ይበላሉ) በወሬያቸው መሀል፣ ሰውዬው አንገቱን ወደ ብርሃኑ በኩል ጣል እያደረገ፣

“ያ ክልስ ከማንኛችሁ ጋር ነው ፍቅር የያዘው? በመጣሁ ቁጥር …” ዐረፍተ ነገሩን ሳይጨርስ አፉን እንደከፈተ ቀረ። ትርሲት የቢራ ጠርሙስ ይዛ ከላዩ ቆማ እንደ ቁጣ አምላክ ትገላምጠዋለች።

“ያንቺ ነው እምዬ?” አላት ደንግጦ።

ስትናደድ ዓይኗ ያስፈራል። ሳትጮህ፣ ግን በቁጣ፣

“አንት የውሻ ክልስ! ውጣ!” አለችው። የጠርሙሱን አንገት የጨበጠው እጇ ይንቀጠቀጣል። ሰውዬው ፈርቶ ብድግ አለ።

ግን ሲነሳ ጊዜ ትንሽ ሆነችበት። እሱ ቀጭ እንዳለ እሷ ወደ ታች ስታፈጥበት ደነገጠ እንጂ፣ አሁን እሱ ከላይ ሆኖ ወደ ታች ሲያያት ፍርሀቱ ለቀቀው። ተራውን እየገላመጣት በሚያንቋሽሽ ድምፅ፣

“ምን ሆነሻል? ግም ሸርሙጣ!” አላት።

ደግነቱ ይህን ጊዜ ብርሃኑ ከኋላዋ መጥቶ ያዛት። ዓይን ዓይኗን በቀጥታ እያየ ጠርሙሱን ቀስ አድርጎ ከእጇ ነጥቆ ለከበቡሽ እያቀበለ፣

“ምንድን ነው?” አላት።

“ምንም” አለችው።

ገባው፣ ፊቱ ደም ለበሰ። ለማረጋገጥ ያህል ሰውዬውንና እነ ከበቡሽን እያየ፣

“ምንድን ነው?” አለ።

ከበቡሽ “ኧረ የለም፣ እዚህ እኔና አስቴር …”

“ውሸታም!” አላት ለመሳቅ እየሞከረ።

ወደ ነጭነት የሚያደላ ፊቱ አሁን ሳምባ መስሏል። ሰውዬውን፣

“ክልስ አልከኝ መሰለኝ” አለው።

ሰውዬው ግዙፍ፣ ኩሩ ቢጤ ነው። ብርሃኑን በንቀት እያየ፣

“ኧ … በእውነቱ ወንድም”

“ወንድምህ አይደለሁም። ክልስ ብለኸኛል?”

“ብልህስ?”

“ትችላለህ። ግን እሷን ግም ሸርሙጣ ስትላት የሰማሁህ መሰለኝ”

“ብላትስ?”

“አትችልም። እሷን እንዳንተ ያለ ግም አቃጣሪ አይሰድባትም”

አስቴር “ብርሃኑ” ብላ ልትይዘው ስትል መነጨቀና ወደዚያ ገፋት። ክበቡሽ ደንግጣ አፈገፈገች። ትርሲት እንደቆመች ቀረች። ሌሎቹ ሴቶች እውስጥ እራታቸውን ይበላሉ። ማንም ሌላ ሰው የለም። ሙዚቃው ይዘፍናል።

ሰውየው “ንፍጣም ክልስ! ሴቶቹ ያግዙልኛል ብለህ ነው መቼስ እንዲህ ሰው እምትደፍረው” አለው።

ብርሃኑ “ለምን ሴቶች የሌሉበት አንሄድም?” አለው።

“ማን ቀድሞ ይውጣ?” አለ ሰውዬው።

“እኔ”

“ሽንታም ክልስ! ልትፈተለኪ ፈልገሽ ነው?”

“እሺ አንተ ቀድመህ ውጣ”

“ቅዘናም ነጭ! በጓሮ ልትሸሺ! እግሬ አውጪኝ ልትይ? መች አጣንሽ?”

“ኦ-ዎህ! እሺ አብረን እንውጣ”

“ሴቶቹ አይፈቅዱልሽማ!”

ብርሃኑ ቃል ሳይጨምር ወደ በሩ ሄደና መጋረጃውን ከፍቶ ጠበቀው። አብረው ወጡ። ብርሃኑ እዚችው አጥር ግቢ ውስጥ ያለችውን ትንሽ ሜዳ እያሳየ፣

“እዚህ ትፈልጋለህ?” አለው።

“ሴቶቹ መጥተው እንዲያግዙልሽ ነው?”

ካጥር ግቢው ወጡና ባቡር መንገድ ሲደርሱ ብርሃኑ፣

“እዚህስ?” አለው።

“ገላጋይ አይጠፋም። ወይ የማሚት እሹሩሩ ዘበኞች ተልከው ይመጡና ያግዙልሻል”

ብርሃኑ ተበሳጨ። ሊያለቅስ ምንም አልቀረው።

“ታዲያ የት እንሂድ?”

“እንጃልህ!” አለው ሰውዬው።

“ጊዮርጊስ ጓሮ እንሂድ?”

“እሺ ምን ከፋኝ?”

ወደ ጊዮርጊስ በኩል ትንሽ እንደተራመዱ ሰውየው ቆመ፣

“አህ! ገባኝ ለካ! …” አለ።

“ምኑ?” አለ ብርሃኑ።

“ጊዮርጊስ ጓሮ ወስደህ በማጅራት መቺ ልታስመታኝ አቅደህ ነው። እኔ ግን እንደዚህ በቀላሉ አልታለልም። መልአኩ ይጠብቀኛላ!”

ብርሃኑ ስልችት አለው።

“እንዲዋጣልን ትፈልጋለህ ወይስ አትፈልግም?” አለው።

“አልፈልግም”

ብርሃኑ በመገረም፣

“ለምን?” አለ።

“ንጹሕ አየር ሲመታኝ ጊዜ ሴጣኔ አለፈልኝ”

ብርሃኑ ዝም አለ።

“ሴጣናም ነኝ ልንገርህ። ሴጣኔ ሲመጣ የሚመልሰኝ የለም። አምስት ስድስቱን ከመሬት ጋር ደባልቄ ቤቴ የምገባበት ጊዜ አለ። ታዲያ ሴጣኔ ሲያልፍልኝ የሠራሁት ሥራ ይቆጨኛል። የገዛ ሀገሬን ልጆች፣ የገዛ ወንድሞቼን መደብደቤ ኃይለኛ ፀፀት ያሳድርብኛል። አንተ ግን እድለኛ ነህ። ሴጣኔ ቶሎ ለቀቀኝ”

“ሴጣንህ ክልስ ሲያይ ይፈራል እ?”

“ይቅርታ አድርግልኝ ወንድሜ። በውነቱ ለክፉ ያልኩት አልነበረም”

ብርሃኑ ይሄ ሰውዬ ሌሎችንም ክልሶች እንደሚያስቸግር ታየው። ስለዚህ እንደ አብዛኞቹ ጉረኞች ፈሪ መሆኑን አውቆ እንዲህ አለው።

“ሰማህ ወንድም፣ ለወደፊቱ ክልሶችን ለማጥቃት ባትሞክር ይሻልሃል። ምክንያቱም የምታየው ክልስ ሁሉ (ከኔ ጭምር) ገና ከሕፃንነቱ ጀምሮ እንዳንተ ያሉ ደደቦች ‘ክልስ! አህያ መልስ! እየበዳህ አልቅስ!’ እያሉ ሲያበሳጩት እየተደባደበ ያደገ ስለሆነ ጥል እንጀራው ነው። ሩቅ ሳንሄድ እኔን ተመልከት። ብትፈልግ እንወራረድና፣ አልቢትሮ ጠርተን፣ እንዳንተ ያሉ ሌሎች ሁለት ጨምረህ፣ ሦስታችሁ ለብቻዬ ኑልኝ። አፈር አስገባችኋለሁ። አስተውል፣ ጉልበት ስላለኝ አይደለም። ክልስ በመሆኔ መደባደብ በግዴታ ስለተማርኩ ነው። ገባህ? በል አሁን እንመለስና ልጅቷን ይቅርታ ለምናት”

“ኧ … ሰማህ ወንድም፣ ምንስ ቢሆን …”

“ወይም ይዋጣልን”

“ምንስ ብሳሳት፣ ራሴው በድዬ ሰው አስቀይሜ ይቅርታ ሳልጠይቅ የምሄድ ሰው እመስላለሁ እንዴ?”

ከዚያ ተመለሱና ሰውዬው ትርሲትን ይቅርታ አድርጊልኝ ብሎ ቢራ ጋበዛት። ብርሃኑም ቢራ ጋብዞት፣ ሲያወራላቸው አምሽቶ ሄደ እልሃለሁ። ከዚያ ማታ ወዲህ እዚህ በመጣ ቁጥር ትርሲትን ጠርቶ “እሳተ ጎመራይቱ! ዛሬ ምን ልጋብዝሽ?” ብሎ አንድ ቢራ ሳይጋብዛት አይሄድም።

ያን ዕለት ማታ ጥላሁን ማሚት እሹሩሩን አስፈቅዶ ወይም አስገድዶ ትርሲትንና ብርሃኑን ቀ.ኃ.ሥ ቲያትር ናይት ክለብ ወሰዳቸው። እና ብርሃኑ “ከትርሲት ጋር ደንስ” አለው።

“የለም፣ እናንተ ስትደንሱ ደስ ይለኛል። የሚዋደዱ ሰዎች ሳይ፣ እንደ’ናንተ ያለ እውነተኛ ፍቅር ሳይ ልቤ በደስታ ይሞታል – ይመታል ማለቴ” አለና የሁለቱንም እጅ ይዞ ሳመ። ሰክሯል … “ደስ ትሉኛላችሁ” አለ።

ትርሲት “ደስ ካልንህ ከኛ ጋር ለምን አትደንስም?” አልችና አስነሳችው። ሲደንስ ጠጋ አደረጋት። ሲቆምበት ተሰማት። አፈረች። እሱም አፈረ። የበለጠውን እያስጠጋት፣

“ትርሲትዬ ይቅርታ አድርጊልኝ” አላት … “ሰክሬያለሁ። ፀጉርሽ ብቻ ሳይሆን ጸባይሽም ጭምር ደስ ይለኛል። ስለዚህ ይቅርታ ካላረግሽልኝ ኩነኔ እገባለሁ። አንቺ ጥሩ ልጅ ነሽ። እኔ ግን ውሻ ነኝ። ከሰከርኩ ከእህቴም ጋር ብደንስ ይቆምብኛል። ብቻ እህት የለኝም። እህቴ አንቺ ነሽ። ግን ልቤ ንጹሕ ነው። ቁላዬ ያልተቆነጠጠ ባለጌ ሆኖ ነው’ንጂ፣ እኔስ እንደ እህቴ ነው የማይሽ። ተቀየምሽኝ?”

“የለም”

“ጥሩ ልጅ ነሽ። እኔ’ኮ ‘ሚቆምብኝ የድሮው ትዝ እያለኝ ነው። አደራ ለብርሃኑ እንዳትነግሪው”

“አልነግረውም”

ከናይት ክለቡ ሲወጡ በጣም ሰክሮ ስለነበረ፣ ከተማውን እንዳይረብሽና እሱም አደጋ ላይ እንዳይወድቅ በማለት ከኛ ጋር እደር አሉት።

“ከናንተ ጋር ባድር ደስ ይለኛል። ከናንተ ጋር ባድር ኩራት ይሰማኛል። ከናንተ ጋር ባድር ከፍቅር ጋር እንዳደርኩ እቆጥረዋለሁ። ከናንተ ጋር ባድር ከናንተ ከወጣቶቹ ጋር አድራለሁ። ከናንተ ጋር ባድር …” አላቸው።

ቤት ሲደርሱ መሀላቸው ደግፈውት አንገታቸውን አቅፎ ተራ በተራ ጉንጫቸውን እየሳመ፣

“በጣም በጣም ነው እምወዳችሁ፣ እዚች ዓለም ላይ እንደ’ናንተ እምወደው የለም። መፋቂያዬስ?” እያለ ወደ ቤት ገቡ።

ትርሲትን መሀል አርገዋት ተኙ።

ሩብ ሰዓት ካለፈ በኋላ ብርሃኑ ቀስ ብሎ “ጥላሁን” አለ። መልስ የለም። ጥላሁን ተኝቷል ማለት ነው። ቀስ ብለው መተቃቀፍና መተሻሸት ጀመሩ።

“ትርሲትዬ!”

“ወዬ የኔ ብርሃን!”

“ሻሽሽን አውልቂልኝ”

“እምቢዮ!”

“እባክሽን!”

“ቆንጆ አርገህ ሳመኝና” ሲባባሉ …

“ቃ!” አለና ድንገት መብራቱ በራ። ጥላሁን ማብሪያውን እንደ ቀይ ሲጋራ በጣቶቹ መሀል ይዞ፣ ደም የለበሱ ጉልህ ዓይኖቹን ክፍት ክድን እያደረገ …

“እኔ ምላችሁ” አለ “እንደዚህ ሆናችሁ ፍቅራችሁን ስትገላለጹ ቁላችሁና እምሳችሁ የቱ የማን እንደሆነ ይታወቃችኋል?” መኖሩን ረስተው ስለነበር ከመደንገጣቸው የተነሳ እንደተቃቀፉ ትንፋሻቸውን እንደዋጡ ቀሩ።

“ማለቴ፣ ከመዋደዳችሁ የተነሳ ቁላው የማንኛችሁ እምሱስ የማንኛችሁ እንደሆነ አይጠፋችሁም ወይ?”

“ምን ማለትህ ነው?” አለ ብርሃኑ

“አየህ ብርሃኑ፣ እንደዚህ ነው። እኔ ፍቅር ፍለጋ ላይ ነው ያለሁት። የፍቅር አዳኝ ይሉሃል ማን ነው? ጥልዬ ነው። ሌላ መልስ የለውም። ፍቅር ማለት እንግዲህ ምንድን ነው? አንድ መሆን ነው። አንድ ታውቅ የለ? ሁለት መሆን ቀርቶ አንድ ትሆናላችሁ። አንድ። የምትተቃቀፉት ለዚህ ነው። አንድ ስትሆኑ እንግዲህ ቁላውም የሁለታችሁ ነው፣ እምሱም የሁለታችሁ ነው። ገባህ?”

ብርሃኑ ዝም ሲል ጊዜ …

“እኔ ‘ምፈልገው ፍቅር ነው። ፍቅር። አስናቀችን ስበዳት በጣም ጣፍጧት በኀይል ስታቅፈኝ፣ ‘ምንድነው ሚገባብሽ?’ ስላት ‘መርዘኛው ቁላህ ነዋ ጥልዬ!’ ትለኛለች። እበሽቃለሁ። እኔ የምፈልገው ‘ቁላችን ነዋ!’ እንድትለኝ ነበር። ‘ይሄ እምስ የማን ነው?’ ስላት ‘ያንተ ነዋ!’ ትለኛለች … ‘የኛ ነዋ!’ እንደማለት። ገባህ? ዳሩ ምን ይገባሃል? ቁላ ሲነሳ አንጎል ይተኛል።”

“ትርሲትዬ፣ ይቅርታ አርጊልኝ ስላቋረጥኳችሁ” አለ።

ቀጥሎ፣

“መፋቂያዬን ጣልኳት ወይስ አስቀመጥኳት? ያለ ‘ሷ ምን ዘመድ አለኝ?” አለና መብራቱን አጥፍቶ ተኛ …

.

ስብሐት ገብረ እግዚአብሔር

(1960ዎቹ)

.

[ምንጭ]“ሌቱም አይነጋልኝ” [እንደወረደ]። ፲፱፻፺፰ ዓ.ም። ገጽ 48-56።

 

One thought on ““ሌቱም አይነጋልኝ” (ልብወለድ)

አስተያየት ለመስጠት

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s